በ21ኛ ሳምንት በመጀመሪያ የተደረገው የባህርዳር ከተማ እና ጅማ አባጅፋር ጨዋታ በጅማ አባጅፋር የ2 – 0 አሸናፊነት ተጠናቋል ።
ባህር ዳር ከተማዎች በ20ኛው ሳምንት ከመከላከያ አቻ በተለያዩበት ጨዋታ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ አራት ለውጦችን ያደረገ ሲሆን መናፍ ዐወል ፤ አህመድ ረሺድ ፤ አሊ ሱሌማን ፤ አብዱልከሪም ኒኪማን በግርማ ዲሳሳ ፤ ሳለአምላክ ተገኝ ፤ ፋዐድ ፈረጃ እና ምትክ ያሰለፉ ሲሆን ጅማ አባጅፋር ደግሞ በሳምንቱ ከኢትዮጵያ ቡና ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ 11 ሁለት ለውጦችን በማድረግ እያሱ ለገሰን እና ወንድማገኝ ማርቆስን በበላይ ዐባይነህ እና ዳዊት ፍቃዱ ምትክ አሰልፈዋል ።በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ ባህርዳር ከተማዎች በተሻለ እንቅስቃሴ ጨዋታውን መጀመር የቻሉ ቢሆንም በፈጣን አጨዋወት ወደ ግብ ለመድረስ የሚጥሩት ጅማ አባጅፋሮች የግብ ሙከራዎችን በማድረግ ቀዳሚ ነበሩ ።
በ7ኛው ደቂቃ ላይ መሀመድኑር ናስር ከግራ አቅጣጫ የተላከለትን ኳስ ወደ ግብ በቀጥታ ሞክሮት የባህርዳር ከተማው ግብ ጠባቂ ፋሲል ገብረሚካኤል አድኖበታል ።
በግብ ሙከራዎች ያልታጀበው ጨዋታ ቀጣዩን የግብ አጋጣሚ ያስመለከተን በ28ኛው ደቂቃ ላይ ሲሆን በባህርዳር ከተማ በኩል ፍፁም አለሙ በቀኝ በኩል ይዞ የገባውን ኳስ ወደ መሀል መቀነስ ችሎ የነበረ ቢሆንም ከሪም ኒኪማ ሳይደርስበት ቀርቷል ።በተለይም ከውሀ እረፍት መልስ ባህርዳር ከተማዎች ከግራ መስመር በሚነሱ ኳሶች የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ቢሞክሩም የተሳካ የግብ ሙከራን ለማድረግ አልቻሉም ። ይባሱኑም በአጋማሹ መጠናቀቂያ ደቂቃ ላይ ግብ አስተናግደዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በቀኝ መስመር በኩል ሄኖክ ኢሳይያስ በእዮብ አለማየሁ ላይ በሰራው ጥፋት የተገኘውን የቅጣት መስዑድ መሀመድ ሲያሻማው አስጨናቂ ፀጋዬ በግንባር በመግጨት በባህርዳር ከተማ መረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል ። የመጀመሪያው አጋማሽም በጅማአባጅፋር የ 1 – 0 መሪነት ተጠናቋል ።በሁለተኛው አጋማሽ ባህርዳር ከተማዎች የማጥቃት ሀይላቸውን በማጠናከር ወደ ተጋጣሚያቸውን የግብ ክልል በመድረስ ጥሩ ጥሩ የግብ ሙከራዎችንም ማድረግ ችለዋል ።
በአጋማሹ የነበሩ የመጀመሪያ ሙከራዎች በ58ኛው ደቂቃ ላይ በተከታታይ የታዩ ሲሆን የጅማ አባጅፋሩ ግብ ጠባቂ አላዛር ማርቆስ የሳለአምላክ ተገኝን ፤ የሄኖክ ኢሳይያስን እና የተመስገን ደረሰን ኳሶች በተከታታይ በማዳን አስደናቂ ብቃት አስመልክቷል ።
ከአንድ ደቂቃ በኋላም ፍፁም አለሙ ከሳጥን ውጪ ያደረገውን ሙከራ በመመለስ ተመልካቾችን ማስጨብጨብ ችሏል ።
ጅማ አባጅፋሮች የባህርዳር ከተማን እንቅስቃሴ ከነሱ የሜዳ ክፍል ጀምሮ ለማቋረጥ ጥረቶችን ያደረጉ ሲሆን አልፍ አልፎ በመልሶ ማጥቃት ወደ ጣና ሞገዶቹ የሚወስዷቸው ኳሶች አስደንጋጭ ነበሩ ።በ62ኛ ደቂቃ ላይም መስዑድ መሀመድ ኳሱን ከፍ አድርጎ ለሱራፌሎ ዐወል የላከለት ኳስ በሱራፌል አማካኝነት ወደ ግብ ተሞክሮ የፈቱዲን ጀማል ኳሱን መጭረፍ ተደምሮበት የጅማ አባጅፋርን መሪነት ወደ 2 – 0 አሳድጓል ።
ይህም የጅማ አባጅፋሮችን በራስ መተማመን ሲጨምር ለባህርዳር ከተማዎች ቀጣዮቹን ደቂቃዎች ከባድ አድርጎታል ። አሰልጣኝ አብርሃም መብራቱ የተጫዋቾች ለውጥን ማድረግ ቢችሉም ውጤቱን የሚቀይርላቸው ሁነኛ ተጫዋች ማግኘት አልቻሉም ።በ76ኛው ደቂቃ ላይ አሊ ሱሌማን ከሰለሞን ወዴሳ በረጅም የደረሰውን ኳስ አረጋግቶ ወደ ግብ መሞከር ቢችልም በዕለቱ ድንቅ የነበረው አላዛር ማርቆስ አድኖታል ።
በመጨረሻም ጅማ አባጅፋር ጨዋታውን በ2 – 0 አሸናፊነት ደምድሟል ።
ውጤቱን ተከትሎ ጅማ አባጅፋር ነጥቡን 15 ማድረስ የቻለ ሲሆን በደረጃው ላይ ግን ለውጥ ያላደረገ ሲሆን ባህርዳር ከተማ በ25 ነጥብ በነበረበት 9ኛ ደረጃ ለይ የሚቆይ ይሆናል ።በ22ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ( ባህርዳር ) በመጪው ግንቦት 2 ( ማክሰኞ ) ባህርዳር ከተማ ወላይታ ድቻን ሲገጥም ሁለት ቀን ቀደም ብሎ ሚያዝያ 30 ( ዕሁድ ) ጅማ አባጅፋር አርባምንጭ ከተማን የሚገጥም ይሆናል ።