በሁለተኛ ሳምንት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የመጨረሻ ጨዋታ ሀዋሳ ከተማ ኢትዮጵያ ቡናን አሸንፏል።
በዉጤት ደረጃ ለሁለቱም ቡድኖች ወሳኝ በነበረዉ ጨዋታ የመጀመሪያውን የግብ ሙከራ በማድረግ ረገድ ቡናማዎቹ ቀዳሚ ነበሩ ፤ በዚህም በ4ኛዉ ደቂቃ ላይ ኤርትራዊው አማካይ ሮቤል ተ/ማርያም ያቀበለዉን ኳስ አብዱልከሪም ወርቁ ያመከናት ኳስ በቡናማዎቹ በኩል አስቆጭ ነበረች። ከደቂቃዎች በኋላም የመስመር ተጫዋቹ ጫላ ተሽታ ያሻገረለትን ኳስ በግንባሩ በመግጨት ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሱ ወደ ዉጭ ወጥቷል።
- ማሰታውቂያ -
በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች ላይ ምንም እንኳን ኢትዮጵያ ቡና በሙከራ ረገድ ጥሩ የነበረ ቢሆንም አስደንጋጭ ነገርን መመልከት አልቻልንም ነበር ፤ በተቃራኒው ጥሩ ለመጫወትም ሆነ ግልፅ የግብ እድል ለማግኘት ሲቸገሩ የነበሩት ሀይቆቹ በ33ኛዉ ደቂቃ ላይ የመጀመሪያ ሙከራቸዉን እና ቀዳሚ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም አዲሱ አቱላ ከመስመር ያሻገረዉን ኳስ ሙጅብ በግንባር በመግጨት ወደ ግብ ሲሞክር የተመለሰውን ኳስ በጥሩ አቋቋም ላይ ይገኝ የነበረዉ አብዱልባሲጥ ከማል አስቆጥሮ ሀዋሳ ከተማን መሪ ማድረግ ችሏል።
ሀይቆቹ መሪ መሆን ከቻሉ በሆላ በይበልጥ በመነቃቃት የጨዋታዉን ቴንፖ ለመቆጣጠር ሲጥሩ ሲስተዋል በተቃራኒዉ ከግቧ መቆጠር በኋላ ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ ጥረት ሲያደርጉ የነበሩት ኢትዮጵያ ቡናዎች በአጋማሹ መገባደጃ ላይ ተጭነዉ መጫወት ችለዉ የነበረ ቢሆንም ነገር ግን ኳስ እና መረብን ማዋሀድ ሳይችሉ ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
ከእረፍት መልስ በተመሳሳይ የጨዋታ መንገድ በቀጠለው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም እምብዛም ተጠቃሽ ሙከራ ባይኖርም በቡናማዎቹ በኩል በጥሩ ቅብብል ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል ለመድረስ ሲጥሩ የተስተዋለ ቢሆንም የሀይቆቹን የተከላካይ መስመር ጥሰዉ ግብ ለማስቆጠር ግን ሲቸገሩ ተስተውሏል።
በተቃራኒው መሪነታቸውን አስጠብቀዉ ለመዉጣት በሚመስል መልኩ በጥንቃቄ መጫወትን የመረጡት ሀዋሳ ከተማዎች አልፎ አልፎ በሚገኙ የቆሙ ኳሶች እና በመልሶ ማጥቃት ተጨማሪ ግብ ለማግኘት ሲምክሩ ታይቷል።
በተለይ በሀዋሳ ከተማ በኩል የአጥቂ አማካዩ ወንድማገኝ ሀይሉ ያሻገረለትን ኳስ በጥሩ አቋቋም ላይ ይገኝ የነበረዉ አሊ ሱለይማን ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ በመሆንም ግብ ጠባቂዉ በረከት አማረ እንደምንም ያወጣት ኳስ እጅግ ለግብ የቀረበች ሙከራ ነበረች። በድጋሚ በ65ኛዉ ደቂቃ ላይ የተገኘዉን የቅጣት ምት ኤፍሬም አሻሞ አክርሮ ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ሲሆን በድጋሚ በግብ ጠባቂዉ በረከት ጥረት ወጥታለች።
በዚህ ሂደት የቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም ዘጠና ደቂቃው ተጠናቆ በጭማሪ ደቂቃ ላይ ሁለት ግቦች ተስተናግደውበታል። በዚህም በ90+2 ላይ ከኤፍሬም አሻሞ የተሻገረለትን ኳስ ተባረክ ሄፋሞ በግንባር በመግጨት ወደ ግብነት ቀይሮ የሀይቆቹን መሪነት ወደ ሁለት ከፍ ማድረግ ችሏል። ከሁለት ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ብሩክ በየነ ከአስራት ቱንጆ የተሻገረለትን ኳስ በግንባሩ በመግጨት አስቆጥሮ ጨዋታዉ በሀዋሳ ከተማ 2ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
በቀጣይ ሀዋሳ ከተማ ከ ጋር ሲገናኙ ኢትዮጵያ ቡና ደግሞ ከወልቂጤ ከተማ ጋር የሚጫወቱ ይሆናል።