በዕለቱ ሁለተኛ ጨዋታ የተገናኘቱ ድሬደዋ ከተማ እና ባህርዳር ከተማ 0 ለ 0 በሆነ ውጤት ተለያይተዋል ።
ድሬዳዋ ከተማዎች በ12ኛው ሳምንት ከአርባምንጭ ከተማ አቻ በተለያዩበት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ ሁለት ቅያሪዎችን ያደረጉ ሲሆን አቤል ከበደን እና ብሩክ ቃልቦሬን በማሳረፍ ዳንኤል ሀይሉን እና ማማዱ ሲዳቤን ያስገቡ ሲሆን ባህርዳር ከተማዎች ደግሞ ሀዋሳ ከተማን ካሸነፉበት ቋሚ አሰላለፍ ሶሰት ለውጦችን በማድረግ መናፍ አወልን ፣ ግርማ ዲሳሳን እና ፍቅረሚካኤል አለሙን በፈቱዲን ጀማል ፣ አህመድ ረሺድ እና አለልኝ አዘነ ተክተው ጨዋታውን ጀምረዋል ።
ድሬዳዋ ከተማዎች የተሻለ በተንቀሳቀሱበት የመጀመሪያ አጋማሽ በኳስ ቁጥጥሩም ብልጫውን በመውደስ ጥሩ ጥሩ የግብ ዕድሎችን መፍጠር ችለው ነበር ። በተለይም ከመስመር ወደ ግብ ወደ ሳጥን በሚሻገሩ ኳሶች ግብ ለማግኘት የሞከሩ ሲሆን በአንፃሩ በባህርዳር ከተማ በኩል በተወሰኑ አጋጣሚዎች በፈጣን ሽግግር ወደ ተጋጣሚያቸው የግብ ክልል መድረስ የቻሉባቸውን አጋጣሚዎች መፍጠር ችለው ነበር ።
- ማሰታውቂያ -
በድሬዳዋ ከተማ በኩል ማማዱ ሲዲቤን ኢላማ ያደረጉ ኳሶች በአየር ላይ ቢላኩለትም የባህርዳሩ ግብ ጠባቂ ፋሲል ገብረሚካኤል እየወጣ ኳሶቹን ሲመልስ ነበር ። በ23ኛው ደቂቃ ላይ ማማዱ ሲዲቤ ከሙኸዲን ሙሳ የደረሰውን ኳስ ለማስቆጠር ሞክሮ በፋሲል ሲመለስ ኳሱን ለግቡ ቅርብ ሆኖ ያገኘው ዐወት ገብረሚካኤል በግንባር ገጭቶ ለማስቆጠር ያደረገው ጥረት ኳሹ ኢላማውን ባለመጠበቁ ሳይሳካ ቀርቷል ።
ብልጫ የተወሰደባቸው የጣና ሞገዶቹ 38ኛ ደቂቃ ላይ በፈጣን ሽግግር ኒኪማ ያገኘውን ኳስ ለአሊ ሱሌማን ቢያቀብለውም በአሊ የተመታው ኳስ ከግቡ አናት በላይ ወጥቷል ። የመጀመሪያው አጋማሽ መጠናቀቂያ ደቂቃዎች ላይ የድሬዳዋ ከተማው አምበል ዳንኤል ደምሴ በጠንካራ ምት አከታትሎ ወደ ግብ የላካቸው ኳሶች በባህርዳር ተካለካዮች ተመልሰው የማዕዘን ምት ሆነዋል ።
የሁለተኛው አጋማሽ የጨዋታ ጊዜ ያን ያህል ሳቢ ያልነበረ እና በሁለቱም በኩል ቀዝቀዝ ያለ እንቅስቃሴ የተደረገበት ነበር ። ባህርዳር ከተማዎች በተለይም በአሊ ሱሌማን አማካኝነት ወደ ሳጥን ሰብረው በመግባት የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ጥረቶችን ማድረግ ችለው የነበረ ቢሆንም ያን ያህል ውጤታማ አልነበሩም ። በአንድ አጋጣሚ አሊ ከግራ መስመር ተነስቶ ወደ ሳጥን ሲገባ ጥፋት የተሰራበት ቢሆንም የዕለቱ ዳኛ ጨዋታው እንዲቀጥል አድርገዋል ።
በድሬደዋ ከተማ በኩል ወደ ፊት በመሄዱ ረገድ ከመጀመሪያው አጋማሽ የተወሰነ መቀነስ አሳይተው ነበር ። በ60ኛ ደቂቃ ላይ ሙኽዲን ሙሳ ከመናፍ አወል የነጠቀውን ኳስ ወደ ግብ ሞክሮት ኳሱ ኢላማውን ሳይጠብቅ ቀርቷል ። በአጋማሹ በሁለቱም በኩል የተደረጉ ጠንካራ የግብ ሙከራዎች ያልተስተዋሉ ሲሆን በድሬዳዋ ከተማ በኩል በ64ኛ ደቂቃ ላይ መኽዲን ሙሳ በባህርዳር ከተማ በኩል ደግሞ 69ኛ ደቂቃ ላይ አለልኝ አዘነ ከሳጥን ውጪ የሞከሯቸው ኳሶች ወደ ውጪ ወጥተዋል ።
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በተጨማሪ ደቂቃ ላይ ግርማ ዲሳሳ መሀመድ አበዱለጢፍ ላይ ጥፋት መስራቱን ተከትሎ የዕለቱ የመሀል ዳኛ በቀጥታ የቀይ ካርድ ከሜዳ ያሰናበቱት ሲሆን ተጫዋቹ በውድድር ዓመቱ የተመለከተው ሁለተኛ የቀይ ካርድም ሆኗል ። በጥፋቱ የተገኘውን የቅጣት ምት ዳንኤል ሀይሉ ወደ ግብ ሞክሮት የግቡ ቋሚ መልሶበት ወጥቷል ። በመጨረሻም ሁለቱም ክለቦች አንድ አንድ ነጥብ ተጋርተው ጨዋታው ተጠናቋል ።
ውጤቱን ተከትሎ ድሬዳዋ ከተማ ነጥቡን 16 ማድረስ ቢችልም ደረጃው ባለበት 11ኛ ሲቆይ ባህርዳር ከተማ በበኩሉ በ18 ነጥብ ወደ 5ኛ ደረጃ ከፍ ብሏል ።
በ14ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ድሬዳዋ ከተማ አዳማ ከተማን ባህርዳር ከተማ ደግሞ ሰበታ ከተማን የሚገጥሙ ይሆናል ።