የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ 26ኛ ሳምንት ሁለተኛ ቀን የመጀመሪያ ጨዋታ ረፋድ 4 ሰዓት ሲል ኢትዮጵያ ቡናን ከአዳማ ከተማ አገናኝቶ በቡናማዎቹ 2ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
በዉጤት ረገድ ለሁለቱም ክለቦች ወሳኝ በነበረዉ ጨዋታ ገና በመጀመሪያው ደቂቃ ላይ ግብ ተስተናግዶበታል። በ2ኛዉ ደቂቃ ላይ ከተከላዩ አዲስ በረጅሙ የተሻገረለትን ኳስ አሜ መሐመድ በፍጥነት አፈትልኮ በመዉጣት ከተቆጣጠረ በኋላ ወደ ግብ ክልል ደርሶ ኳስና መረብን በማገናኘት ክለቡን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ከግቧ መቆጠር በኋላ በ7ኛዉ ደቂቃ ላይ በድጋሚ ከመሀል ተከላካዩ አዲስ የተሻገረለትን ኳስ የመስመር አጥቂዉ አብዲሳ ጀማል በፍጥነት ሮጦ ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል ደርሶ የነበረ ቢሆንም አጥቂው የሞከራት ኳስ በግቡ አናት ላይ ለጥቂት ወጥታለች።
በጨዋታዉ መባቻ ላይ ግብ ካስተናገዱ በኋላ ወደ ጨዋታው ለመመለስ የተቸገሩ ይመስሉ የነበሩት ቡናማዎቹ በ11ኛዉ ደቂቃ ላይ ተከላካዩ ቶማስ ስምረቱ አቡበከር ናስር ላይ ጥፋት መስራቱን ተከትሎ የተገኘዉን የቅጣት ምት ወጣቱ አጥቂ ወደ ግብ ቢሞክርም ኳሷ ለጥቂት ወጥታበታለች።
ከዉሀ ዕረፍት መልስ በሁለቱም ቡድኖች በኩል ተመጣጣኝ የሚባልን የጨዋታ እንቅስቃሴን መመልከት የቻልን ሲሆን በተለይ በ34ኛዉ ደቂቃ ላይ ከአቤል እንዳለ የተሻገረለትን ኳስ አጥቂዉ አቡበከር በግንባሩ በመግጨት ወደ ግብ ቢሞክርም የግቡን አግዳሚ ነክታ ወደ ዉጭ የወጣችዉ ኳስ እጅግ ለግብ የቀረበ ድንቅ ሙከራ ነበር።
በተለይ ከመጀመሪያው አጋማሽ የዉሃ ዕረፍት መልስ በመከላከሉ ረገድ ተሻሽለዉ የተመለሱት ቡናማዎቹ የአዳማ ከተማን የማጥቃት ጥንካሬ ተቋቁመዉ ተጨማሪ ግብ ሳያስተናግዱ ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
ከአጋማሹ መልስ የመጀመሪያውን አስር ደቂቃዎች ያህል የተሻሉ የነበሩት አዳማ ከተማዎች ተደጋጋሚን ሙከራ ማድረግ የቻሉ ቢሆንም ተጨማሪ ግብ ግን ማስቆጠር አልቻሉም ነበር። በተለይ በ51ኛዉ ደቂቃ ላይ የመስመር ተጫዋቹ አቡበከር ወንድሙ ጥሩ የግብ እድል አግኝቶ የነበረ ቢሆንም ሳይጠቀምበት ቀርቷል። ከደቂቃዎች በኋላ ደግሞ የቡድን አጋሩ አሜ መሐመድ በድጋሚ ግልፅ የግብ ዕድልን ቢያገኝም ግብ ጠባቂዉ በረከት አማረ ደርሶበት መጠቀም ሳይችል ቀርቷል።
በ69ኛዉ ደቂቃ ላይ የመስመር አጥቂዉ አላዛር ሽመልስ ከአዳማ ከተማ ተከላካይ የነጠቀዉን ኳስ ለአቡበከር ናስር በጥሩ አመቻችቶ አቀብሎት አቡበከርም በአንድ ንክኪ ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል።
በድጋሚ በ77ኛዉ ደቂቃ ላይ ከአስራት ቱንጆ የተቀበለዉን ኳስ አጥቂዉ አቡበከር ናስር የግል ብቃቱን ተጠቅሞ የአዳማ ከተማ ተከላካዩቹን አታሎ በማለፍ ለራሱ እና ለክለቡ ሁለተኛዉን ጎል በማስቆጠር ክለቡ ኢትዮጵያ ቡና ሁለት ለአንድ እንዲመራ ማድረግ ችሏል።
አዳማ ከተማዎች በጨዋታው መገባደጃ ወቅትም በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ቀይረዉ ወደ ሜዳ ማስገባት ቢችሉም ተጨማሪ ግብ ማግኘት ሳይችሉ ቀርተዉ ጨዋታዉ በቡናማዎቹ 2ለ1 አሸናፊነት ተጠናቋል።
ዉጤቱን ተከትሎም ኢትዮጵያ ቡና በ40 ነጥብ ሶስተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ በአንፃሩ አዳማ ከተማ ደግሞ በ30 ነጥብ 11ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል።