በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 13ኛ ሳምንት የሁለተኛ ቀን ውሎ የመጀመሪያ ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡናን ከአርባምንጭ ከተማ አገናኝቶ 51ኛ ደቂቃ ላይ በበላይ ገዛኸኝ በተቆጠረ ብቸኛ ግብ አርባምንጭ ከተማዎች ደረጃቸውን ያሻሻሉበትን ድል አስመዝግበዋል ።
ኢትዮጵያ ቡናዎች በ12ኛ ሳምንት አዲስ አበባ ከተማን በረቱበት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ የሶሰት ተጨዋቾች ቅያሪ ያደረጉ ሲሆን በወንድሜነህ ደረጃ ፣ ሮቤል ተክለሚካኤል እና አቡበከር ናስር ምትክ ቴዎድሮስ በቀለን ፣ አቤል እንዳለን እና እንዳለ ደባልቄን ያስገቡ ሲሆን በሳምንቱ ከድሬዳዋ ከተማ አቻ የተለያዩት አርባምንጭ ከተማዎች ደግሞ በጨዋታው ከነበረው ቋሚ 11 ሁለት ቅያሪዎችን በማድረግ ኡቸና ማርቲንን እና ሀቢብ ከማልን በበርናንድ ኦቼንጌ እና ራምኬል ሎክ ተክተው አስገብተዋል ።
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ አብዛኛው የኳስ ፍሰት በኢትዮጵያ ቡና የሜዳ ክልል ላይ የቆየ ሲሆን ቡናማዎቹ እንደተመደመው ኳሱን ከኋላ መስርተው በመውጣት ለመጫወት ያደረጉት ጥረት በአርባ ምንጭ ከተማ ተጫዋቾች ጫና መፍጠር ምክንያት በተደጋጋሚ ኳሶችን በመነጥቅ እና በራሳቸው ላይ አደጋ ሊፈጥሩ የሚችሉ ኳሶችን የጋበዙ ነበር ። አዞዎቹ የቡናማዎቹ ምስረታ ከግብ ክልላቸው ሳይረቅ በመቀማት ጥሩ ጥሩ የግብ ዕድሎችን መፍጠር ችለዋል ።
- ማሰታውቂያ -
ጨዋታው ገና አንደኛው ደቂቃ እንኳን ሳይሞላ በአርባ ምንጭ ከተማ በኩል ኤሪክ ካፓይቶ ከበላይ ገዛኸኝ የደረሰውን ኳስ በአግባቡ ሳይጠቀምበት ቀርቷል ። በ3ኛው ደቂቃ ቁቃይ ፀጋዬ አበራ ከቀኝ መስመር ወደ ግብ ክልል ያሻገረውን ኳስ ቴዎድሮስ በቀለ በእጁ ቢነካውም የዕለቱ ዳኛ በዝምታ ያለፉት ሲሆን ከሁለት ደቂቃዎች በኋላም ፀጋዬ ከሳጥን ውጫ አክርሮ የመታው ኳስ በአቤል ማሞ ተመልሶበታል ።
በኢትዮጵያ ቡና በኩል ከኋላ የሚመሰረተው ኳስ ብዙም ሳይርቅ ከመነጠቁ በተጨማሪ ከግብ ጠባቂው አቤል ማሞ ለቡድን አጋሮቹ የሚላኩ ኳሶች ያሰበበት ቦታ ሳይደርሱ በአርባ ምንጭ ከተማ ተጨዋቾች ይነጠቁ የነበረ ሲሆን በተለይም 17ኛ ደቂቃ ላይ አቤል ግቡን ለቆ ወጥቶ ለስዩም ለማቀበል የሞከረው ኳስ በፀጋዬ አበራ ተነጥቆ የነበረ ቢሆንም ወደ ግብ የተሞከረው ኳስ ኢላማውን ሳይጠብቅ ወደ ውጪ ሊወጣ ችሏል ።
ከውሀ እረፍት መልስ 27ኛ ደቂቃ ላይ በላይ ገዛኸኝ በሳጥን ውሰጥ ሆኖ ያገኘውን ኳስ ወደ ግብ ለመሞከር ያደረገው ጥረት ኳሱ ኢላማውን ባለመጠበቁ ሳይሳካ ቀርቷል ። ቡናማዎቹ በተወሰነ መልኩ ቀድሞ ከነበረው በተሻለ ወደ ፊት ለመሄድ የተንቀሳቀሱ ቢሆንም የአርባ ምንጭ ከተማ የግብ ክልል መድረስ እንደ ሰማይ እርቋቸው ነበር ።
በጨዋታው 41ኛ ደቂቃ ላይ ዊልያም ሰለሞን ጉዳት ማስተናገዱን ተከትሎ ሚኪያስ ሰለሞን ተክቶት የገባ ሲሆን ተጫዋቹ ለተጨማሪ ህክምና ወድያው ወደ ሆስፒታል ተወስዷል ። የመጀመሪያው አጋማሽም ያለ ምንም ግብ ተጠናቋል ።
የሁለተኛው አጋማሽ በፈጣን እንቅስቃሴ የተጀመረ ሲሆን አሁንም ዕድሎችን በመፍጠር አዞዎቹ የበላይ ነበሩ ። በዚህም 51ኛው ደቂቃ ላይ በላይ ገዛኸኝ ኤሪክ ካፓይቶ በረጅም የተላከለትን ኳስ በደረቱ አረጋግቶ ያቀበለው ኳስን ፊት ለፊት ከግብ ጠባቂው ጋር ተገናኝቶ በማስቆጠር አርባ ምንጭ ከተማን ቀዳሚ አድርጓል ።
በኢትዮጵያ ቡና በኩል 62ኛ ደቂቃ ላይ የቡድኑን ቁልፍ ተጫዋች አቡበከር ናስርን እና ሮቤል ተክለሚካኤል ቀይረው ያስገቡ ቢሆንም ወደ ራሳቸው ሜዳ በማፈግፈግ ጥቅጥቅ ብለው የሚጫወቱትን የአርባ ምንጭ ከተማ ተጫዋቾች አልፈው የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር በእጅጉ ተቸግረው ነበር ። አርባ ምንጭ ከተማዎች ከኳስ ኋላ በቁጥር በዝተው በመገኘት በሚነጠቁ ኳሶች ፈጣን መልሶ ማጥቃት ዕድሎችን ለመፍጠር ጥረቶችን ያደረጉ ሲሆን በ79ኛው ደቂቃ ላይ ሙና በቀለ የኢትዮጵያ ቡና ተከላካዮችን ስህተት ተጠቅሞ በፍጥነት ወደ ሳጥን ገብቶ ኳስን ከመረብ ለማገናኘት ያደረገው ሙከራ ሳይሳካለት ቀርቷል ።
በመጨረሻም አዞዎቹ ሙሉ ሶሰት ነጥቡን ይዘው ወጥተዋል ።
ውጤቱን ተከትሎ አርባ ምንጭ ከተማ ነጥቡን 16 በማድረስ ወደ 8ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ኢትዮጵያ ቡና በ18 ነጥብ ወደ 7ኛ ደረጃ ለመንሸራተት ተገዷል ።
በ14ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ኢትዮጵያ ቡና ፋሲል ከተማን አርባምንጭ ከተማ ደግሞ ቅዱስ ጊዮርጊስን የሚገጥሙ ይሆናል ።