በ17ኛው ሳምንት የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛ ቀን ውሎ በቀዳሚነት የተደረገው የፋሲል ከተማ እና ወልቂጤ ከተማ ጨዋታ ከእረፍት በፊት በተቆጠሩ ግቦች ወልቂጤ ከተማ 2 – 1 በሆነ ውጤት ፋሲል ከተማን ረቷል ።
ፋሲል ከተማዎች በ16ኛው ሳምንት ጨዋታ ከሀድያ ሆሳዕና ጋር ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ከነበረው አሰላለፍ ሁለት ቅያሪዎችን ያደረጉ ሲሆን በይድነቃቸው ኪዳኔ እና ኦኪኪ አፎላቢ ምትክ ሳማኪ ሚካኤልን እና ሱራፌል ዳኛቸውን ጨዋታውን እንዲጀምሩ ያደረጉ ሲሆን ወልቂጤ ከተማዎችም ከአዳማ ከተማ ጋር ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ላይ ከነበረው ምርጥ 11 ሁለት ለውጦችን በማድረግ ረመዳን የሱፍ እና አክሊሉ ዋለልኝን በዳግም ንጉሴ እና ያሬድ ታደሰ ተክተው አሰገብተዋል ።የመጀመሪያው አጋማሽ በሁለቱም በኩል ጥሩ የማጥቃት አጨዋወት እና ጥሩ ፉክክር ያስመለከተን ነበር ። ፋሲል ከተማዎች በኳስ ቁጥጥሩ ብልጫ በመውሰድ ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል በመድረሱ ረገድ የተሻሉ ቢመስሉም ወልቂጤ ከተማዎች በፈጣን መልሶ ማጥቃት ወደ ፊት በሚያልፉበት ጊዜ ከአፄዎቹ የተሻለ አደገኛ የግብ ዕድሎችን መፍጠር ችለው ነበር ።
ገና በሁለተኛው ደቂቃ ሽመክት ጉግሳ ከበረከት ደስታ የደረሰውን ጥሩ ኳስ ወደ ግብ ሞክሮት የወልቂጤ ከተማው ግብ ጠባቂ ሰዒድ ሀብታሙ ያመከነበት ሲሆን ከሶስት ደቂቃዎች በኋላም ጌታነህ ከበደ ከጫላ የተቀበለውን ኳስ መሞከር ቢችልም ኳሱ ኢላማውን የጠበቀ አልነበረም ።ፋሲሎች ኳሱን ይዘው ወደ ወልቂጤ ከተማ የግብ ክልል ለመድረስ እና ለማስከፈት ጥረቶቾን በሚያደርጉበት ጊዜ ወልቂጤ ከተማዎች አከታትለው ሁለት ግቦችን አስቆጥረውባቸዋል ። በ17ኛው ደቂቃ ላይ አብዱልከሪም ወርቁ ከሳጥን ውጪ ወደ ግብ የመታው ኳስ በሳማኪ ሲመለስ በቅርብ የነበረው ጫላ ተሺታ ኳሱን አግኝቶ ከመረብ ላይ አሳርፎታል ። ከአንድ ደቂቃ የቡድኑ አምበል በኋላም ከያሬድ ባየህ የቀማውን ኳስ ተጠቅሞ የወልቂጤ ከተማን ሁለተኛ ግብ ማስቆጠር ችሏል ።
ከግቦቹ መቆጠር በኋላ አፄዎቹ ቀድሞ ከነበረውም በተሻለ የተጋጣሚያቸውን የተከላካይ ክፍል ለመፈተን ጥረቶችን አድርገው ነበር ። በ24ኛው ደቂቃ ላይም ሙጂብ ቃሲም ከሱራፌል ዳኛቸው ያገኘውን ኳስ ወደ ግብ ቢልከውም ሰይድ አድኖበታል ። ማጥቃታቸውን አጠናክረው የቀጠሉተ ፋሲል ከተማውች በ35ኛው ደቂቃ ላይ ኳስ እና መረብን የሚያዋድድላቸው ተጫዋች አግኝተዋል ። ተጫዋቹም ሽመክት ጉግሳ ሲሆን በሳጥን ውሰጥ ሆኖ ከሙጂብ የደረሰውን ኳስ በማስቆጠር የጨዋታውን ውጤት ወደ 2 – 1 መለወጥ ችሏል ። ከግቡ መቆጠር አምስት ደቂቃዎች በኋላም ሱራፌል ዳኛቸው ከቆመ ኳስ በቀጥታ ወደ ግብ የላከው ሙከራ በሰይድ ግብ ከመሆን ድኗል ። የመጀመሪያው አጋማሽ በወልቂጤ ከተማ መሪነት ተጠናቀቀ ።
በሁለተኛው አጋማሽ በመመራት ላይ የነበሩት የአሰልጣኝ ስዩም ከበደ ልጆች ጫና መፍጠራቸውን የቀጠሉበት ነበር ። በወልቂጤ ከተማ በኩል ደግሞ የሚገኙ ኳሶችን ለፊት አጥቂው ጌታነህ ከበደ በማድረስ የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር ጥረቶችን ማድረግ ችለው ነበር ።
ምንም እንኳን በብዙ ነገር የበላይነቱን አፄዎቹ ወስደው ለማጥቃት ቢሞክሩም የወልቂጤ ከተማ የተከላካይ ክፍል የሚቀመስ ሊሆንላቸው አልቻለም ። ወደ ወልቂጤ ሳጥን የሚላኩ ኳሶች በሙሉ ግብ ጠባቂው ጋር ሳይደርሱ ይመለሱ ነበር ።በወልቂጤ ከተማ በኩል በ71 እና 82ኛው ደቂቃ ላይ በጫላ ተሺታ እና ጌታነህ ከበደ አማካኝነት ተጨማሪ ግብ ለማግኘት ያደረጓቸው ሙከራዎች በሳማኪ ሚካኤል ግብ ከመሆን ድነዋል ።
- ማሰታውቂያ -
በመጨረሻም የአሰልጣኝ ተመስገን ዳናው ቡድን ከጨዋታው ሙሉ ሶሰት ነጥብ ይዞ መውጣት ችሏል ።
ውጤቱን ተከትሎ ወልቂጤ ከተማ ነጥቡን 24 በማድረስ ወደ 6ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ፋሲል ከተማ በበኩሉ በ27 ነጥቦ በነበረበት 4ኛ ደረጃ ላይ የሚቆይ ይሆናል ።
በ18ኛው ሳምንት ጨዋታዎች ፋሲል ከተማ በመጪው ረቡዕ ቀን 9 ሰዓት ላይ ጅማ አባጅፋርን ሲገጥም ባህርዳር ከተማ በቀጣዩ ቀን ምሽት 12 ሰዓት ላይ ድሬዳዋ ከተማን ይገጥማል ።