በአሰልጣኝ ጥላሁን ተሾመ እየተመሩ በታሪካቸዉ ለመጀመሪያ ጊዜ በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ተሳትፎን ማድረግ የቻሉት ለገጣፎ ለገዳዲዎች የመጀመሪያ ጨዋታቸዉን በድል ተወጥተዋል።
በዋና ዳኛ ተካልኝ ለማ ፊሽካ የተጀመረዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታ የመጀመሪያዎቹን አስራአምስት ደቂቃዎች ያህል ተመጣጣኝ ፉክክር ተመልክተንበታል ማለት ይቻላል። በተለይ የጨዋታው ሰዓት እየገፋ በመጣ ቁጥር ወደ ሪትማቸዉ በመግባት ጥሩ መንቀሳቀስ የቻሉት ክትፎዎቹ ተደጋጋሚ ሙከራዎችን ማድረግ ችለዉም ነበር ፤ በዚህም በተለይ ከቀኝ መስመር በኩል የተገኘዉን ቅጣተ ምት ዳንኤል ደርቤ ሲያሻማዉ ግዙፉ አጥቂ ሙጅብ ቃሲም ወደ ግብ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም በግብ ዘቡ ወንደሰን አማካኝነት ኳሷ ወጥታለች።
በጨዋታዉ መባቻ ደቂቃ ላይ እንደ ቡድን ጥሩ የነበሩት ለገጣፎዎች ቀስ በቀስ በሀይቆቹ ብልጫ ሊወሰድባቸዉ ችሏል። በዚህም በተለይ በ26ኛዉ ደቀቃ ላይ አዲሱ አቱላ ያሻገረለትን ኳስ ኤርትራዊዉ አጥቂ አሊ ሱለይማን ወደ ግብነት ቀይሮ ሀይቆቹን መሪ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ከግቧ መቆጠር በኋላ በይበልጥ የጨዋታ ብልጫ መዉሰድ ችለዉ የነበሩት ሀዋሳ ከተማዎች በ31ኛዉ ደቂቃ ላይ በድጋሚ ግብ ለማስቆጠር ከጫፍ ደርሰዉ ነበር ፤ በዚሁ ደቂቃ ላይም የመስመር ተከላካዩ ዳንኤል ደርቤ ያሻገረለትን ኳስ ኤፍሬም አሻሞ ቢያገኛትም አምክኗታል። ከዚህ ሙከራ በኋላም አጥቂው አሊ ሱለይማን በድጋሚ ግብ ለማስቆጠር ተቃርቦ የነበረ ቢሆንም ሳይሳካለት ቀርቷል።
የጨዋታው የደት እየገፋ በመጣ ቁጥር መቀዛቀዝ ይታይባቸዉ የነበሩት ለገጣፎዎች የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች በቀሩበት ወቅት ግን አቻ መሆን የቻሉበትን ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም በ42ኛዉ ደቂቃ ላይ ኪሩቤል ያሻማዉን ኳስ አጥቂዉ ካርሎስ ዳምጠዉ በግምባሩ በመግጨት ወደ ግብነት ቀይሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል። በዚህም የመጀመሪያው አጋማሽ አንድ እኩል በሆነ ዉጤት ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ ሀይቆቹ በአጥቂያቸዉ አሊ ሱለይማን እና ሙጅብ ቃሲም በተደጋጋሚ የግብ ሙከራ ማድረግ ሲችሉ ፤ በተቃራኒው ለገጣፎዎች የፊት መስመር አጥቂያቸዉን ካርሎስ ዳምጠዉን መሰረት ያደረጉ ረጃጅም ኳሶችን በመላክ ከጨዋታዉ አንዳች ነገርን ለመፍጠር ሲታትሩ ተስተውሏል። በዚህም ጣፎዎች ዉጥናቸዉ ሰምሮ በ61ኛዉ ደቂቃ ላይ የሀዋሳ ከተማዉ ተከላካይ ላዉረንስ ላርቴ ኳሷን በግንባሩ ለግብ ጠባቂዉ መሀመድ ሙንታሪ ለማቀበል ሲጥር ግዙፉ አጥቂ በመሀል ደርሶ ኳሷን ወደ ግብነት በመቀየር ለገጣፎን መሪ ማድረግ ችሏል።
ከግቧ መቆጠር በኋላ በዕለቱ ድንቅ ሲንቀሳቀስ የነበረዉ አጥቂዉ ካርሎስ ዳምጠዉ ለራሱም ለክለቡም ሶስተኛ ግብ ለማስቆጠር የሚችልበትን ተደጋጋሚ ዕድል አግኝቶ የነበረ ቢሆንም ሳይጠቀምባቸዉ ቀርቷል። በአንፃሩ በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ጥሩ ሲንቀሳቀሱ እና መሪ መሆን ችለዉ የነበሩት ሀይቆቹ የኋላ ኋላ በተቆጠሩባቸዉ ግቦች ቢመሩም አቻ ለመሆን በሁሉም ረገድ ሲጥሩ የነበረ ቢሆንም በጨዋታዉ ተጨማሪ ግብ ማግኘት ሳይችሉ ቀርተዉ በአዲስ አዳጊዉ ለገጣፎ ለገዳዲ 2ለ1 በሆነ ዉጤት ተሸንፈዋል።
በቀጣይ ለገጣፎ ለገዳዲ ከድሬዳዋ ከተማ ጋር ሲገናኙ በተመሳሳይ ሀዋሳ ከተማ ደግሞ ከኢትዮጵያ ቡና ጋር የሚጫወቱ ይሆናል።