በጅማ አባጅፋር እና ሲዳማ ቡና መካከል የተደረገው የ12ኛ ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ የመጨረሻ ጨዋታ በሲዳማ ቡና የ 2 ለ 0 አሸናፊነት ተጠናቋል ።
ጅማ አባጅፋሮች በ11ኛ ሳምንት ጨዋታ ሀድያ ሆሳዕናን ሲያሸንፉ የተጠቀሙትን ቋሚ አሰላለፍ ምንም ሳይቀይሩ የገቡ ሲሆን ሲዳማ ቡና ከአርባ ምንጭ ከተማ አቻ በተለያዩበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ አስራአንድ ሁለት ቅያሪዎችን ያደረጉ ሲሆን ተስፋዬ በቀለን እና ዳዊት ተፈራን በጊት ጋትኩት እና ብሩክ ሙሉጌታ ምትክ ጨዋታውን እንዲጀምሩ አድርገዋል ።
ጨዋታው ገና ከጅምሩ በፈጣን እንቅስቃሴዎች ታጆቦ ኳሶችም በፍጥነት ወደ ግብ ክልል የሚደርሱበት ነበር ። ሲዳማ ቡና በአንፃራዊነት ኳሱን በመቆጣጠር እና ወደ ፊት በመሄድ ከተጋጣሚያቸው የተሻሉ ነበሩ ።
- ማሰታውቂያ -
18ኛው ደቂቃ ላይ የሲዳማ ቡና የመስመር ተከላካይ መሀሪ መና ወደ ግብ ያሻገረውን ኳስ የጅማ አባጅፋር ግብ ጠባቂ በአግሩ ለማውጣት ሲሞክር ስህተት ሰርቶ ግብ ሊያስተናግድ ነበር ። ከአስር ደቂቃዎች በኋላ ይገዙ ቦጋለ ከጅማ ተከላካዮች የነጠቀውን ኳስ ለዳዊት ተፈራ አቀብሎ መልሶ የደረሰውን ኳስ በአግባቡ በመጠቀም የሲዳማ ቡና የመጀመሪያ ግብ አስቆጠረ ።
ጅማ አባጅፋሮች በተወሰኑ አጋጣሚዎች በመልሶ ማጥቃት ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ለመድረስ ያደረጓቸው ጥረቶች ስኬታማ ያልነበሩ ሲሆን የመጀመሪያው አጋማሽም ሌላ ግብ ሳያስተናግድ በሲዳማ ቡና መሪነት ተጠናቋል ።
በሁለተኛው አጋማሽ ጅማ አባጅፋሮች በተሻለ መነቃቃት የጀመሩት ቢሆንም ከአጋማሹ ጅማሮ ጥቂት ደቂቃዎች ውስጠሰ ነበር ሌላ ግብ ያስተናገዱት ። ኢያሱ ለገሰ በሳጥን ውስጥ በይገዙ ቦጋለ ላይ በሰራው ጥፋት ምክንያት የተገኘውን የፍፁም ቅጣት ምት ዳዊት ተፈራ 51ኛ ደቂቃ ላይ አስቆጥሮ የሲዳማ ቡና መሪነትን ከፍ አደረገ ።
ጅማ አባጅፋሮች የማጥቃት የበላይነቱን በመውሰድ ግብ ለማስቆጠር ጥረቶችን ቢያደርጉም ኳስን ከመረብ የሚያገናኝላቸው ተጫዋች ማግኘት አልቻሉም ነበር በአንፃሩ ሲዳማ ቡናዎች በፈጣን ሽግግሮች የግብ ዕድሎችን ለመፍጠር የሞከሩ ቢሆንም ውጤቱ በሁለት ለዜሮ ውጤት ተጠናቋል ።
ውጤቱን ተከትሎ ሲዳማ ቡና ነጥቡን 18 በማድረስ ወደ 5ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ጅማ አባጅፋር በ7 ነጥብ የሊጉ ግርጌ ላይ የሚቆይ ይሆናል ።
በ13ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ሲዳማ ቡና ወልቂጤ ከተማን ጅማ አባጅፋር ደግሞ ወላይታ ድቻን የሚገጥሙ ይሆናል ።