የአስረኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ሁለተኛ ጨዋታ ከምሽቱ አንድ ሰዓት ጀምሮ በሲዳማ ቡና እና በባህርዳር ከተማ መካከል ተካሂዶ ከእረፍት በፊት ባስቆጠሩት ግብ ሲመሩ የነበሩት ባህርዳር ከተማዎች ከእረፍት በኋላ በተቆጠሩባቸው ሁለት ግቦች ሽንፈት አጋጥሞቸዋል ።
ዋና አሰልጣኛቸውን አብርሀም መብራቱን በአፍሪካ ዋንጫ ምክንያት ማግኘት ባለመቻላቸው በምክትል አሰልጣኛቸው እየተመሩ ወደ ጨዋታው የገቡት የጣና ሞገዶቹ በዘጠነኛው ሳመንት ጨዋታ ከተጠቀሙት ቋሚ አሰላለፍ የአራት ተጫዋቾች ቅያሪ በማድረግ አቡበከር ኑሪ ፤ አሀመድ ረሺድን ፤ በረከት ጥጋቡን እና ተመስገን ደረስን ያሰለፉ ሲሆን በሲዳማ ቡና በኩል ወላይታ ድቻን የገጠመው ቋሚ አሰላለፍ ምንም ሳይቀይሩ ወደ ጨዋታው መግባት ችለዋል ።
- ማሰታውቂያ -
ጨዋታው ከጅምሩ ፈጣን እንቅስቃሴ የታየበት እና በሁለቱም በኩል በቶሎ ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ለመድረስ ጥረቶች የተደረጉበት ነበር ። በሶስተኛው ደቂቃ ላይ የባህርዳር ከተማው አሊ ሱሌማን በረጅም የተሻገረለትን ኳስ ወደ ግብ ለመቀየር ያደረገውን ሙከራ ግብ ጠባቂው ተክለማርያም ሻንቆ ወቶ መልሶበታል ። ከአምስት ደቂቃዎች በኋላም ፍፁም አለሙ ከግራ መስመር ላይ የተሳገረለትን ኳስ አሊ አስቆጠረው ተብሎ ሲጠበቅ ኳሱ ከግቡ አናት በላይ ወጥቶበታል ።
በሲዳማ ቡና በኩል በተለይም በሳጥኑ የቀኝ መስመር ላይ ይገዙ ቦጋለ ወደ ግብ የሞከራቸው ኳሶች ኢላማቸውን መጠበቅ አልቻሉም ነበር ። 21ኛ ደቂቃ ላይ ፍሬው ሰለሞን ከተከላዮች ጀርባ አምልጦ በመግባት ከዳዊት ተፈራ የደረሰውን ኳስ ለመቆጣጠር ሲሞክር ግብ ጠባቂው አቡበከር ኑሪ ሲመልስበት ይገዙ ቦጋለ አግኝቶ ወደ ግብ ቢሞክረውም ግብ ጠባቂው በድጋሚ መልሶታል ።
30ኛ ደቂቃ ላይ ፍፁም አለሙ በቀኝ መስመር ላይ ሁለት የሲዳማ ቡና ተጫዋቾችን በማለፍ ለኒኪማ አቀብሎ ጥሩ ቦታ በመገኘት መልሶ የደረሰውን ኳስ ወደ ግብ በመምታል የባህርዳር ከተማን ቀዳሚ ግብ አስቆጠረ ። ከግቡ መቆጠር ሁለት ደቂቃዎች በኋላ በሲዳማ ቡና በኩል ሀብታሙ ገዛኸኝ ከሳጥን ውጪ ወደ ግብ የመታው ኳስ በግብ ጠባቂው አቡበከር ግብ ከመሆን ድኗል ። የመጀመሪያው አጋማሽም በጣና ሞገዶቹ መሪነት ተጠናቀቀ ።
በሁለተኛው አጋማሽ ሲዳማ ቡናዎች በተሻለ የተንቀሳቀሱበት ነበር ። ጥረታቸውም የማታ ማታ ፍሬ አፍርቶላቸዋል ።
የግብ ሙከራዎች በቀላሉ ያልተስተናገዱበት ሁለተኛው አጋማሽ በ69ኛ ደቂቃ ላይ ግብ አስተናግዷል ። በዳዊት ተፈራ ተቀይሮ የገባው ብሩክ ሙሉጌታ ገና ወደ ሜዳ ከገባ በሰከንዶች ውስጥ ቴዎድሮስ ታፈሰ ያሻገረውን ኳስ በመጀመሪያ ንክኪው ወደ ግብነት መቀየር ችሏል ። ከግቡ በኋላ ባህርዳር ከተማዎች በተወሰነ መልኩ የመነቃቃት ሁኔታ ቢያሳዩም ብዙም ሳይገፉበት በሲዳማና ቡና ብልጫ ተወስዶባቸው ተጨማሪ ግብ ለማስተናገድ ተገደዋል ።
መደበኛው የጨዋታ ጊዜ ሊጠናቀቅ ሁለት ያህል ደቂቃዎች ሲቀሩት ሀብታሙ ገዛኸኝ ከፍሬው ሰለሞን የተሰነጠቀለትን ኳስ ከግቡ ትየዩ ነፃ ሆኖ ሲጠብቀው ለነበረው ይገዙ ቦጋለ አቀብሎት አጥቂው ኳሱን ከመረብ አዋህዶታል ።
በመጨረሻም ሲዳማ ቡና ጨዋታውን 2 ለ 1 አሸንፎ ወጥቷል ።
ውጤቱን ተከትሎም ሲዳማናዘ ቡና ነጥቡን 14 በማድረስ ወደ 6ኛ ደረጃ ከፍ ሲል ባህርዳር ከተማ ደግሞ ተመሳሳይ 14 ነጥብ ቢኖረውም በግብ ክፍያ ወደ 5ኛ ደረጃ ተንሸራቷል ።