በአዲሱ አሰልጣኛቸው ገብረክርስቶስ ቢራራ እየተመሩ የዉድድር አመቱን የመክፈቻ ጨዋታ መከወን የቻሉት ወልቂጤ ከተማዎች በፊት መስመር አጥቂያቸዉ ጌታነህ ከበደ ብቸኛ ግብ ተጋጣሚያቸውን የመሳይ ተፈሪዉን አርባምንጭ ከተማ ማሸነፍ ችለዋል።
አሰልጣኝ ገብረክርስቶስ ቢራራ በክረምቱ የተጫዋቾች የዝውውር መስኮት ክለቡን ከተቀላቀሉት ተጫዋቾች መካከል ዘጠኝ ያህሉን በመጀመሪያ አስራአንድ ማሰለፍ ሲችሉ በአንፃሩ አዞዎቹ አርባምንጭ ከተማዎች ደግሞ ከአዳዲስ ፈራሚወቹ መካከል አራት ያህሉን በቋሚ አስራ አንድ ዉስጥ አካተዉ ጨዋታቸውን ከዉነዋል።
ለአይን ማራኪ በነበረዉ የሁለቱ ክለብች ጨዋታም ገና በጨዋታው መባቻ ላይ ለግብ የቀረበ ሙከራን ተመልክተንበታል። በተለይ በ7ኛዉ ደቂቃ ላይ ጌታነህ ከበደ ከርቀት በቅጣት ምት ወደ ግብ የላካት ኳስ በክትፎዎቹ በኩል አስቆጭ ሙከራ ነበረች። ከዚች ሙከራ በኋላም በይበልጥ የኳስ ቁጥጥር የበላይነቱን በመዉሰድ በተደጋጋሚ ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል ሲደርሱ የነበሩት ክትፎዎቹ በድጋሚ በ38ኛዉ ደቂቃ ላይ ለግብ የቀረበ ሙከራን ማድረግ ችለዉ ነበር ፤ በዚሁ ደቂቃም የመሐል ተከላካዩ ዉሀብ አዳምስ ከማዕዘን የተሻገረዉን ኳስ በግምባር በመግጨት ግብ ለማስቆጠር ከጫፍ ደርሶ የነበረ ቢሆንም ሳይሳካ ቀርቷል።
- ማሰታውቂያ -
በጨዋታው አብዝሀኛዉ ክፍል ላይ ወደራሳቸው የግብ ክልል አፈግፍገዉ ሲጫወቱ የነበሩት አዞዎቹ ምንም እንኳን አልፎ አልፎ በመልሶ ማጥቃት ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል በመግባት ያደርጓቸው ከነበሩ ጥቂት ሙከራዎች ዉጭ ይሄ ተብሎ ሊጠቀስ የሚችል አደገኛ ሙከራ አስመልክተዉናል ማለት አይቻልም። በዚህም የመጀመሪያው አጋማሽ ያለ ግብ 0ለ0 በሆነ ዉጤት ተገባዷል።
ከዕረፍት መልስ ጨዋታዉ ግብ ለማስተናገድ አምስት ደቂቃዎች ብቻ ነበሩ የፈጁበት በዚህም የአርባምንጩ ተከላካይ በርናንድ ኦቺንግ ብዙአየሁ ተስፋዬ ላይ በሰራዉ ጥፋት የተገኘዉን ቅጣት ምት ጌታነህ ከበደ ወደ ግብነት ቀይሮ ክትፎዎቹን መሪ ማድረግ ችሏል።
ከግቡ መቆጠር በኋላ ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት ሲያደርጉ የነበሩት አዞዎቹ በ56ኛዉ ደቂቃ ላይ አቻ ለመሆን ቀርበዉ ነበር በዚሁ ደቂቃ ላይ መላኩ ኤሊያስ የወልቂጤዎቹን የግብ ዘብ መዉጣት ተከትሎ ወደ ግብ የላከዉ ኳስ እንደምንም ወጣበት እንጅ አቻ ለመሆን ተቃርበዉ ነበር ፤ በዚህ ሂድት በቀጠለዉ የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም ተጨማሪ ግብ ሳያስመለከትን በክትፎዎቹ አንድ ለምንም አሸናፊነት ተጠናቋል።
በቀጣይ ወልቂጤ ከተማ ጋር ከባህርዳር ከተማ ጋር የሚገናኙ ሲሆን በአንፃሩ አርባምንጭ ከተማ ደግሞ ከኢትዮጵያ መድን ጋር የሚጫወቱ ይሆናል።