የ18ኛው ሳምንት የመጨረሻ ጨዋታ በወልቂጤ ከነማ እና በባህርዳር ከነማ መካከል ተደርጎ አራት ግቦች ባስተናገደው ጨዋታ ሁለት ሁለት ግቦች አስቆጥረው አቻ ተለያይተዋል ።
ወልቂጤ ከነማዎች በ17ኛው ሳምንት ፋሲል ከነማን ሲረቱ ከነበረው ምርጥ 11 ሁለት ለውጦችን በማድረግ ሮበርት ኦዶንካራን ፣ ዳግም ንጉሴ ፣ ያሬድ ታደሰን እና ዮናስ በርታን በሰይድ ሀብታሙ ፣ ረመዳን የሱፍ ፣ አክሊሉ ዋለልኝ እና ሀብታሙ ሸዋለም ምትክ ሲያስገቡ ባህርዳር ከነማ ደግሞ በሳምንቱ በሀድያ ሆሳዕና በተረቱበት ጨዋታ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ በተመሳሳይ አራት ቅያሪዎችን በማድረግ በአህመድ ረሺድ ፣ አለልኝ አዘነ ፣ አብዱልከሪም ኒኪሚያ እና ተመስገን ደረሰ ምትክ መሳይ አገኘሁ ፣ ፍፁም አለሙ ፣ አደም ሀባስ እና ግርማ ዲሳሳን ተክተው ጨዋታውን ጀምረዋል ።በምሽቱ ጨዋታ ወልቂጤ ከተማዎች ገና በጅምሩ በጌታነህ ከበደ ባደረጉት የግብ ሙከራ ጨዋታውን መጀመር ችለዋል ። ቀጣዩ ወልቂጤ ከነማዎች ያደረጉት የግብ ሙከራ ግን ከመረብ ላይ ያረፈ ነበር ።
ጨዋታው 5ኛ ደቂቃ ላይ ሲደርስ ያገኙትን የማዕዘን ምት አበባው ቡጣቆ ሲያሻግረው የመሀል ተከላካዩ ዋሁብ አዳምስ በግንባር ገጭቶ በማስቆጠር ቡድኑን መሪ አድርጓል ። ከግቡ በኋላ ባህርዳር ከነማዎች ከፍተኛ የኳስ ቁጥጥር ብልጫ በመውሰድ በተጋጣሚያቸው ላይ ጫና ማሳደር ችለዋል ።የጣና ሞገዶቹ ከፊት መስመር ላይ በተለይም ኦሴይ ማውሊ ኢላማ ያደረጉ ኳሶች ቢያደርሱም የወልቂጤ ከነማ ተከላካዮች ንቁ ሆነው በመጠበቅ ማውሊ ተመቻችቶ ኳሶቹን ማግኘት እንዳይችል አድርገውታል ።
በ29ኛው ደቂቃ ላይ ከማዕዘን በተነሳ ኳስ ማዉሊ ያገኘውን ኳስ በግንባር ገጭቶ ወደ ግብ ቢልከውም ኢላማውን ሳይጠብቅ ሲቀር ከዘጠኝ ደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ፍፁም አለሙ ከግራ መስመር ያሻገረውን ኳስ ፉአድ ፈረጃ አስቆጥረው ተብሎ ቢጠበቅም ኳሱን በአግባቡ ማግኘት ሳይችል ቀርቷል ።
- ማሰታውቂያ -
ወደ ኋላ አፈግፍገው አልፎ አልፎ በመልሶ ማጥቃት እና ረጃጅም ኳሶች ሌላ ግብ ለማከል ሲጥሩ የነበሩት ወልቂጤ ከነማዎች በ43ኛው ደቂቃ ላይ በበሀይሉ ተሻገር ከሳጥን ውጪ ተሞክሮ ለጥቂት ኢላማውን ሳይጠብቅ ከቀረው ኳስ ውጪ ሌላ የግብ ዕድል መፍጠር ሳይችሉ የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቋል ።የጨዋታው ሁለተኛ አጋማሽ ጅማሮ በባህርዳር ከነማዎች በኩል በጥሩ ሁኔታ የተጀመረ ነበር ። አጋማሹ በተጀመረ ሁለተኛው ደቂቃ ላይ በቅጣት ከሜዳ ርቆ የቆየው ግርማ ዲሳሳ ከሳጥን ውጪ በግሩም ሁኔታ ወደ ግብ የላከው ኳስ ከኦዶንካራ መረብ ላይ አርፎ ባህርዳር ከነማን አቻ አደረገ ።
በግቡ የተነቃቁት የጣና ሞገዶቹ ወደ ተጋጣሚያቸው የግብ ክልል በሚሻገሩ ተደጋጋሚ ኳሶች ሌላ ግብ ለማስቆጠር ጥረቶችን አድርገዋል ። በወልቂጤ ከነማ በኩል ከፊት አጥቂው ጌታነህ ከበደ ውጪ አብዛኞቹ ተጫዋቾች በራሳቸው የሜዳ ክፍል ላይ በመቆየት በመከላከሉ ተወጥረው ቆይተዋል ።
በ56 እና 57ኛ ደቂቃዎች ላይ አሊ ሱሌማን እና ፍፁም አለሙ አከታትለው ከሳጥን ውጪ ወደ ግብ የላኳቸው ኳሶች ከቀድሞው የፈረሰኞቹ ግብ ጠባቂ ሮበርት ኦዶንካራ ማለፍ የቻሉ አልነበሩም ። ተደጋጋሚ ተሻጋሪ ኳሶችን ወደ ግብ ሲልኩ የነበሩት ባህርዳር ከነማዎች በ75ኛው ደቂቃ ላይ ከመመራት ወደ መሪነት የመጡበትን ግብ አስቆጥረዋል ።ከማዕዘን የተሻገረ ኳስ በወልቂጤ ከነማ ተከላካዮች ሲመለስ ኳሱን ያገኘው ፍፁም አለሙ ዳግም ወደ ግብ ያሻገረው ኳስ በኦሴ ማውሊ ሲገጭ ከግቡ ትይዩ ነፃ ሆኖ የተገኘው አምበሉ ፍቅረሚካኤል አለሙ ኳስ እና መረብን አገናኝቷል ።
ለተከታታይ አምስት ጨዋታዎች ማሸነፍ ያልቻሉት ባህርዳር ከነማዎች በከፍተኛ ደስታ ላይ ሆነው የጨዋታውን የመጨረሻ ደቂቃ በመጠባበቅ ላይ ሳሉ ጫላ ተሺታ በደስታቸው ላይ ቀዝቃዛ ውሀ ጨምሮበታል ።87ኛ ደቂቃ ላይ በራሱ ላይ በተሰራ ጥፋት የተገኘውን የቅጣት ምት ጌታነህ ከበደ ሲያሻግረው በግንባር በመግጨት የወልቂጤ ከነማን ሁለተኛ ግብ ማስቆጠር ችሏል ። የጣና ሞገዶቹ በተጨማሪ ደቂቃዎች ላይ ለግቡ በቅርብ ርቀት ሁለት የቅጣት ምቶችን ቢያገኙም ወልቂጤ ከነማዎች ኳሱን ለመከላከል የሰሩትን የተከላካይ አጥሮች ያለፉ አልነበሩም ። በመጨረሻም ጨዋታው ሁለት አቻ በሆነ ውጤት ተጠናቋል ።
ውጤቱን ተከትሎ ወልቂጤ ከነማ ነጥቡን 25 በማድረስ 6ኛ ደረጃን መልሶ ሲረከብ ባህርዳር ከነማ ደግሞ በ22 ነጥብ ወደ 10ኛ ደረጃ ከፍ ብሏል ።በ19ኛው ሳምንት ጨዋታዎች ባህርዳር ከነማ በመጪው ረቡዕ አመሻሽ 12 ሰዓት ጀምሮ ከአርባምንጭ ከነማ ሲጫወቱ ወልቂጤ ከነማ ደግሞ ሶስት ሰዓታትን ቀደም ብሎ ከሀዋሳ ከነማ ጋር ጨዋታውን ያደርጋል ።