በ26ኛው ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ የመጨረሻ ጨዋታ በወልቂጤ ከተማ እና መከላከያ መካከል ተደርጎ ግብ ሳያስተናግድ ተጠናቋል ።
ወልቂጤ ከተማዎች በ25ኛው ሳምንት ከሀድያ ሆሳዕና ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ላይ ከነበረው የመጀመሪያ አሰላለፍ አንድ ለውጥ ብቻ በማድረግ ተስፋዬ ነጋሽን በጌታነህ ከበደ ምትክ ሲያሰልፉ በመከላከያ በኩል በሳምንቱ ከድሬዳዋ ከተማ ነጥብ በተጋሩበት ጨዋታ ከነበረው ምርጥ 11 በተመሳሳይ አንድ ለውጥ በማድረግ ገናናው ረጋሳን በግሩም ሀጎስ ምትክ አሰልፈው ጨዋታውን ጀምረዋል ።
የጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ አጀማመሩን ፈጠን አድርጎ ቀስ በቀስ የተቀዛቀዘ የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ የታየበት ነበር ። በአንፃራዊነት የተሻለ ወደ ፊት መድረስ የቻሉት መከላከያዎች በ8ኛው ደቂቃ ላይ በአዲሱ አቱላ አማካኝነት ከሳጥን ውጪ ያደረጉት የግብ ሙከራ በወልቂጤ ከተማው ግብ ጠባቂ ሰይድ ሀብታሙ ተመልሷል ።
በወልቂጤ ከተማ በኩል በፈጣን እንቅስቃሴ እና ጥሩ ጥሩ የአንድ ሁለት ቅብብሎች የተጋጣሚያቸውን የኋላ ክፍል አልፈው ለመግባት ጥረዋል ። በዚህም በጨዋታው ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረው አብዱልከሪም ወርቁ ከቀኝ መስመር አቅጣጫ የመከላከያ ተጫዋቾችን አልፎ ገብቶ የሞከረው ኳስ ለጥቂት ኢላማውን ሳይጠብቅለት ቀርቷል ።
- ማሰታውቂያ -
ቀጣዩ የግብ ሙከራ የታየው በ34ኛው ደቂቃ ላይ ሲሆን አዲሱ አቱላ ከቀኝ መስመር ያሻገረውን ኳስ እስራኤል እሸቱ በግንባር ገጭቶ ወደ ግብ ሞክሮ ሰይድ ሀብታሙ ግብ ከመሆን አድኖበታል ።
በ39ኛው ደቂቃ ላይም በወልቂጤ ከተማ በኩል ጫላ ተሺታ በግራ መስመር ያገኘውን ኳስ ነፃ ለነበረው ተስፋዬ ነጋሽ ያቀብለዋል ተብሎ ሲጠበቅ ወደ ግብ የመታው ኳስ በቀላሉ በክሌመንት ቦዬ ተይዟል ።
የሁለተኛው አጋማሽ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በመጀመሪያው አጋማሽ ተመሳሳይ እንቅስቃሴ የቀጠለ ነበር ።
ወደ ተጋጣሚ የግብ ክልል ደርሶ የግብ ዕድሎችን በመፍጠሩ ረገድ የተሻሉ የነበሩት መከላከያዎች በ52ኛው ደቂቃ ላይ በተሾመ በላቸው አማካኝነት በግንባር ኳስ ወደ ግብ የተሞከረው ኳስ ለጥቂት ወደ ውጪ ወጥቷል ።
በወልቂጤ ከተማ በኩል አልፎ አልፎ በፈጣን እንቅስቃሴዎች ወደ መከላከያ የግብ ክልል ለመድረስ ጥረቶችን ማድረግ ቢቸሉም ጠንከር ያለ የግብ ሙከራ ማድረግ አልቻሉም ነበር ። በማራኪ አንድ ሁለት ቅብብሎች የተጋጣሚያቸውን የኋላ መስመር ሰብረው ለመግባት የሚያደርጓቸው ጥረቶች በተደጋጋሚ ከጨዋታ ውጪ በመሆን ይቋረጡ ነበር ።
የጨዋታው መደበኛ ክፍለ ጊዜ ተጠናቆ በተጨማሪ ደቂቃዎች ላይ ቢንያም በላይ ከሳጥኑ በቅርብ ርቀት የተገኘውን የቅጣት ምት በቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ ሰይድ ሀብታሙ በድንቅ ብቃት ግብ ከመሆን አድኖታል ።
በመጨረሻም ጨዋው ያለግብ ተጠናቋል ።
ውጤቱን ተከትሎ መከላከያ በ32 ነጥብ 9ኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ወልቂጤ ከተማ ደግሞ ነጥቡን 31 በማድረስ 10 ደረጃ ላይ ተቀምጧል ።
በ27ኛ ሳምንት ጨዋታዎች በመጪው ሰኔ 11 (ቅዳሜ ) ረፋድ 4:00 ላይ ወልቂጤ ከተማ የሊጉን መሪ ቅዱስ ጊዮርጊስን ሲገጥም በተከታዩ ቀን ሰኔ 12 ( ዕሁድ ) በተመሳሳይ ሰዓት መከላከያ ከወላይታ ድቻን የሚጫወት ይሆናል ።