በበረሀዋ ንግስት ድሬዳዋ ከተማ በተደረገዉ የቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የስድስተኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን የመጀመሪያ ጨዋታ ባህርዳር ከተማ ኢትዮጵያ መድንን 3ለ2 በሆነ ዉጤት አሸንፏል።
በአሰልጣኝ ደግአረግ ይግዛዉ እየተመራ በአምስት የሊጉ ጨዋታዎች ስምንት ነጥቦችን በመሰብሰብ አምስተኛ ደረጃ ላይ ይገኝ የነበረዉ ባህርዳር ከተማ ከአምስት ሳምንታት የከተማዉ ቆይታ በኋላ በድሬዳዋ ስታዲየም ባለፉት ጨዋታዎች ድንቅ ብቃቱን በማሳየት የሊጉ አናት ላይ መቀመጥ የቻለዉን ኢትዮጵያ መድንን በገጠመበት ጨዋታም ገና በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች ወቅት ተደጋጋሚ ሙከራን መመልከት ችለን ነበር ፤ በዚህም ለአብነት የሚጠቀሰዉ በ10ኛዉ ደቂቃ ላይ ሰላምላክ ተገኝ ያሻገረለትን ኳስ የመስመር አጥቂዉ ሀብታሙ ታደሰ በጭንቅላቱ ሞክሮ የነበረ ቢሆንም ኳሷ ለጥቂት ወጥታለች።
- ማሰታውቂያ -
ምንም እንኳን ተመጣጣኝ የሜዳ ላዬ እንቅስቃሴ በመጨዋታዉ ወቅት ብንመለከትበትም ኢትዮጵያ መድን የመጀመሪያዉን ሙከራ ለማድረግ 34 ያህል ደቂቃዎች ፈጅተዉበታል። በዚህም ከግራ መስመር ተከላካዩ ያሬድ የተሻገረለትን ኳስ የፊት መስመር ተጫዋቹ ብሩክ ሙሉጌታ በጭንቅላቱ ወደ ግብነት በመቀየር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
የአቻነት ግብ ለማግኘት ቶሎ ቶሎ ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል ይደርሱ የነበሩት የጣና ሞገዶቹ በ38ኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ማስቆጠር ችለዋል። በዚህም ከማዕዘን የተሻማዉን ኳስ የመድን ተጫዋቾች በአግባቡ ማራቅ ባለመቻላቸው ምክንያት ተስፋየ ታምራት ከርቀት አስደናቂ ግብ አስቆጥሮ ክለቡን አቻ ማድረግ ችሏል።
ለዕረፍት ወደ መልበሻ ክፍል ከማምራታቸዉ በፊት የጣና ሞገዶቹ ድንቅ የግብ ዕድል መፍጠር ችለዉ ነበር በዚህም በ46ኛዉ ደቂቃ ላይ ሀብታሙ ታደሰ ከተከላካዮች ጋር ታግሎ ያቀበለዉን ግልፅ ኳስ ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
ከዕረፍት መልስ ተሻሽለዉ እና የማጥቃት ሀይላቸውን አጠናክረዉ የተመለሱት ባህርዳር ከተማዎች በ50ኛዉ ደቂቃ ላይ መሪ መሆን የቻሉበትን ግብ አግኝተዋል። በዚህም የመድን ተከላካዮች በቅብብል ወቅት የሰሩትን ስህተት ተከትሎ ፉአድ ፈረጃ ድንቅ ግብ በማስቆጠር ክለቡን መሪ ማድረግ ችሏል።
አሁንም በተደጋጋሚ የመድንን የግብ ክልል መጎብኘት የቀጠለዉ ባህርዳር ከተማ ተጨማሪ ግብ ማስቆጠር ችሏል። በዚህም በ63ኛዉ ደቂቃ ላይ አማካዩ አለልኝ አዘነ ከርቀት አክርሮ የመታዉን ኳስ ግብ ጠባቂዉ ሲመልሰዉ በአቅራቢያው የነበረዉ ሀብታሙ ታደሰ ወደ ግብነት ቀይሮ መሪነታቸውን ወደ ሶስት ከፍ ማድረግ ችለዋል።
የጨዋታው ሰዓት እየገፋ በመጣ ቁጥር የመጣቃት ሀይላቸዉን በመጨመር እና በመልሶ ማጥቃት ወደ ጨዋታዉ ለመመለስ ጥረት ያደርጉ የነበሩት መድኖች መደበኛዉ ዘጠና ደቂቃ ተገባዶ በ92ኛዉ ደቂቃ ላይ በኪቲካ ጀማል አማካኝነት ግብ ማስቆጠር ቢችሉም ጨዋታው በባህርዳር ከተማ 3ለ2 አሸናፊነት ተጠናቋል።