ጋዜጠኛ መሸሻ ወልዴ ሀያ አምስት አመታትን በታማኝነት ላገለገለበት እና ለለፋበት የኢትዮጵያ እግርኳስ እና የጋዜጠኝነት ሙያ የእዉቅና እና የምስጋና ፕሮግራም ለማድረግ ከሁለት ወራት በፊት ዝግጅቱን የጀመረዉ አዘጋጅ ኮሚቴዉ ትላንት ምሽት በሳፋየር አዲስ ሆቴል የክብር እንግዶች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው የስፖርት ቤተሰቦች በተገኙበት ተከናውኗል።
የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርቱን በዳግማዊ ቴዎድሮስ እና የካቲት 23 የተከታተለዉ መሸሻ ወልዴ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን ያጠናቀቀ ሲሆን በኮሌጅ ደረጃ ደግሞ በተግባረ ዕድ የሙያ ትምህርቱን መከታተል ችሏል።
በህትመት ደረጃ ከአስራ ዘጠኝ ዘጠናዎቹ አጋማሽ ጀምሮ ከሰራባቸው ጋዜጦች መካከልም ሻምፒዮና ፣ ማራቶን ፣ ካታንጋ ፣ ይድነቃቸው ፣ አዲስ ስፖርት ፣ ካምቦሎጆ እና ዩኒቲ ኮሌጅ የመሳሰሉት ተጠቃሽ ሲሆን ፤ በተጨማሪም አሁን ላይ በሀገሪቱ በቀሩት ብቸኛ ሁለት ጋዜጦች ማለትም በሊግ ስፖርት እና ሀትሪክ ስፖርት እየሰራ ይገኛል።
- ማሰታውቂያ -
በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዘርፍም በኤፍሬም 90.7 እና ኤፍሬም 96.3 በሀገር ዉስጥ የእግርኳስ ላይ ትኩረት በማድረግ ረዘም ላሉ አመታት መስራት ችሏል።
በአብዛኞቹ የስፖርት ቤተሰቦች ዘንድ የኢትዮጵያ እግርኳስ ላይብረሪ በመባል የሚታወቀው መሸሻ ወልዴ በትላንታው ምሽት በነበረዉ የእዉቅናና የምስጋና ፕሮግራምም ከስድስት መቶ ስልሳ ሺ ብር (660000) በላይ በስጦታ መልክ ተበርክቶለታል።
በዕለቱም የተለዩ የስፖርት ሰዎች አሰልጣኞች ፣ ተጫዋቾች እንዲሁም የጋዜጠኛዉ መሸሻ ወልዴ ፎቶግራፍ በወጣቱ በረከት በስል ተስለዉ ለታዳሚዉ በጨረታ መልክ የቀረቡ ሲሆን። በዚህም በምሽቱ ፕሮግራም ላይ ታዳሚ የነበሩት የከፍተኛ የእግርኳሱ አመራሮች እንዲሁም አሰልጣኞች ተሳታፊ ሆነዉበታል።
ከሌሎቹ የስፖርት ጋዜጠኞች በተለየ መንገድ በወጣቶች እና በሴቶች እግርኳስ ላይ በትኩረት ቃለ-ምልልሶችን በመስራት የሚታወቀዉ መሸሻ ወልዴ በእለቱ ስለተደረገለት የዕውቅና እና የምስጋና ፕሮግራም አስመልክቶ ሀሳቡን እንደዚህ ሲል አስተላልፏል:-
” በመጀመሪያ ይሄንን ፕሮግራም የምስጋና ፕሮግራም ላዘጋጃችሁ ኮሚቴዎች በጣም ላመሰግናችሁ እፈልጋለሁ፤ ለወንዶችም ሴቶችም እግርኳስ ተጫዋቾችም ትልቅ አክብሮት አለኝ በእናንተ ነዉ እና እኔ እዚህ መድረሴ በተጨማሪም በሀገር ዉስጥ እግርኳስ ላይ በትኩረት የሚሰሩትን የስፖርት ዞን ፣ የሀትሪክ እና የሊግ ስፖርት አዘጋጆች ማመስገን እፈልጋለሁ። በጨመረሻም ሁላችንም ከታች ጀምሮ በትኩረት ከሰራን እግርኳሳችንን ማሳደግ እንደምንችል ለመናገር አወዳለሁ አመሰግናለሁ ” ሲል ሀሳቡን አጠቃሏል።