በአምስት ነጥቦች እና ዘጠኝ ደረጃዎች ተበላልጠው አምስተኛ እና አስራ አራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዉ የዕለቱን ሁለተኛ ጨዋታ የጀመሩት ኢትዮጵያ ቡና እና ሲዳማ ቡና ጨዋታቸውን ያለ ግብ በአቻ ዉጤት አገባደዋል።
ምንም እንኳን ከጨዋታው የሚገኘዉ ውጤት ለሁለቱም ቡድኖች ከፍ ያለ ወሳኝነት የነበረዉ ቢሆንም በይበልጥ ግን በወራጅ ቀጠናዉ አስራ አራተኛ ደረጃ ላይ ለተቀመጠዉ ሲዳማ ቡና የዉጤቱ አስፈላጊነት ላቅ ያለ ነበር ፤ በዚህም ባሳለፍነዉ ሳምንት ወልቂጤ ከተማን አንድ ለምንም ማሸነፍ የቻለዉ ኢትዮጵያ ቡና በ4-2-31 አሰላለፍ ወደ ሜዳ ሲገባ በተቃራኒው የአሰልጣኝ ስዩም ከበደ ቡድን ሲዳማ ቡና ደግሞ በ4-3-3 ዳይመንድ አሰላለፍ ጨዋታውን ጀምሯል።
- ማሰታውቂያ -
ምንም እንኳን በጨዋታዉ የመጀመሪያ አጋማሽ ግብ አይስተናገድበት እንጅ ሁለቱም ቡድኖች በተለይ ኢትዮጵያ ቡና በመሐል ሜዳዉ ላይ የተሻለ በመንቀሳቀስ ቶሎ ቶሎ ወደ ሲዳማ ቡና የግብ ክልል በመድረስ ጎል ለማስቆጠር ሲጥር በተቃራኒው ሲዳማ ቡና ደግሞ በመስመር ላይ ያመዘነ የጨዋታ መንገድ በመከተል ከመስመር አጥቂዉን ሳልሀዲን ኢላማ ያደረጉ ኳሶችን ወደ በመላክ ግብ ለማስቆጠር ሲጥሩ የነበረ ቢሆንም ሁለቱም ቡድኖች ጎል ሳያስቆጥሩ የመጀመሪያው አጋማሽ ያለ ግብ ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ ሁለቱም ቡድኖች ጥንቃቄን መሰረት ያደረገ የጨዋታ እንቅስቃሴ በመከተል አልፎ አልፎ በሚገኙ አጋጣሚዎች ጎል ለማስቆጠር ሲጥሩ ተስተውሏል ፤ በተለይ ሲዳማ ቡና በሳልሀዲን ሰይድ ፣ ቡልቻ ሹራ እና ፍሬዉ ሰለሞን ተደጋጋሚ ለግብ የቀረቡ ሙከራዎችን ማድረግ ችለዉ ነበር ፤ በተመሳሳይ ቡናማዎቹም ተከታታይ ድላቸዉን ለማስመዝገብ በይበልጥ ጭነዉ ለመጫወት ሲሞክሩ በተለይ በአጥቂዉ ብሩክ በየነ ፣ መስፍን ታፈሰ እና አልፎ አልፎም በአማካዮቹ አብዱልከሪም እና ሮቤል ለግብ የቀረቡ ጥሩ ጥሩ ሙከራዎችን ማድረግ ቢችሉም ግብ ማስቆጠር ሳይችሉ ቀርተዉ ነጥብ ለመጣል ተገደዋል።
ዉጤቱን ተከትሎም ሲዳማ ቡና ከተከታታይ ሁለት ሽንፈቶች በኋላ ተከታታይ ሁለት የአቻ ዉጤት በማስመዝገብ በ21 ነጥቦች 14ተኛ ደረጃ ላይ ሲቀመጥ ፤ በተቃራኒው ከድል መልስ በዛሬው ጨዋታ አቻ የተለያዩት ቡናማዎቹ በ26 ነጥቦች አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል።