መሀመድ ኑር ኢትዮጵያ ቡናን
ተቀላቅሏል
👉*… ተጨዋቹ ለዝውውሩ 804 ሺህ ብር ወጪ
አድርጓል…
👉ጅማ አባጅፋር ከወጣቱ አጥቂ መሀመድ ኑር ጋር የነበረውን ቀሪ የአንድ አመት ኮንትራት በ800ሺህ ብር ማፍረሱ ተረጋግጧል።
ኢትዮጴያ ቡና ከወራቶች በፊት ከኢትዮጵያ ቡና ጋር ቢስማማም እስከ ዛሬ ጠዋት ድረስ መልቀቂያውን ሳያገኝ በመቅረቱ ዝውውሩ እውን ሳይሆን ቀርቷል። ወደ ከፍተኛ ሊግ የወረደው ጅማ አባጅፋር ከተጨዋቹ ጋር የአንድ አመት ውል ያለው በመሆኑ በ2015 መሀመድ ኑርን ጨምሮ ሁሉንም ውል ያላቸውን ተጨዋቾች የማቆየት መብቱ ነበረው ነገር ግን ተጨዋቹ ወጣት በመሆኑና የእግርኳስ ህይወቱ እንዲያድግ በማሰብ በፕሪሚየር ሊጉ መጫወት እንዲፈቀድለት ለጅማ አባጅፋር አመራሮች ያቀረበው ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ በማግኘቱ ዝውውር የማድረግ ዕድሉን አግኝቷል።
- ማሰታውቂያ -
ይህን ተከትሎ ተጨዋቹን የማስፈረም ዕድላቸውን በውሳኔያቸው ያጡት ኢትዮጵያ ቡናና ቅዱስ ጊዮርጊስ ፈላጊ ክለቦቹ ሆነው ቀርበዋል። ኢትዮጵያ ቡና አምና በ500ሺህ ብር ተጨዋቹን የማግኘት ዕድል ቢኖረውም በወቅቱ የነበሩት አሰልጣኞቹ ከእኛ አጨዋወት ጋር አይሄድም በማለታቸው ሳይሳካ ቀርቷል። ቅዱስ ጊዮርጊሶችም ፈልገውት በወቅቱ የነበረው የውጪ አሰልጣኝ ልየው በማለቱ የምታይበት ደረጃ አልፏል ያለው ተጨዋቹ ወደ አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ጅማ አባጅፋር ማቅናቱ ይታወሳል።
ጅማ አባጅፋር ለተጨዋቹ ዝውውሩን ፈቅዶ ነገር ግን ለዝውውሩ 600ሺህ ብር እንደሚፈልግ በማሳወቁ ኢትዮጵያ ቡና የተጠየቀውን ለመክፈል ፍቃደኛ ይሆናል። ዝውውሩ መፈቀዱን ያዩት ፈረሰኞቹ ዋጋውን ወደ 800 ሺህ ብር ከፍ ያደርጉታል ቡናማዎቹ ፍላጎታቸው የጠነከረ በመሆኑ ተመሳሳይ ገንዘብ ለመክፈል ይስማማሉ ።
ኢትዮጵያ ቡናና ቅዱስ ጊዮርጊስ ገንዘቡን ለመክፈል በመስማማታቸው የተጨዋቹ ፍላጎት መታየት ስለነበረበት ተጨዋቹም ከቤተሰቦቹ ጋር በመነጋገር መጫወት የምፈልገው ለኢትዮጵያ ቡና ነው በማለት ለጅማ አባጅፋር በደብዳቤ ሲገልጽ በጎን የቅዱስ ጊዮርጊስ አመራሮችን በስልክ በማናገር ፍላጎቱን ያስረዳቸዋል። ጊዮርጊሶቹም ተጨዋቹ ለፈረሰኞቹ መጫወት እንደማይፈልግ በመግለጹ ተፈልገን እንጂ የማይፈልገንን ተጨዋች አናስፈርምም በማለት ፍላጎታቸውን እንደተዉ ለተጨዋቹና ለጅማ አባጅፋር በመግለጻቸው የተጨዋቹ ለኢትዮጲያ ቡና የመፈረም ፍላጎት ተሳክቷል።
ተጨዋቹ ዛሬ ጠዋት ለጅማ አባጅፋር የተጠየቀውን 800ሺህ ብር በመክፈል መልቀቂያውን በማግኘቱ ፌዴሬሽን ጽ/ቤት በመገኘት የውል ማፍረሺያ 4000 ብር በመክፈልና ውሉን በመቅደድ ለኢትዮጵያ ቡና ለመጫወት የሁለት አመት ኮንትራቱን ለመፈረም ችሏል።