” በሚገባ አጥቅተን ከተጫወትን ዉጤታማ የማንሆንበት ምክንያት የለበትም። ( possess has to be positive )”
” ግዴታ እራሳችን ስህተት እየሰራን መማር የለብንም ! “
አሰልጣኝ ስዩም ከበደ ከዛሬ ምሽቱ የዋልያዎቹ እና የካሜሩን ጨዋታ አስቀድሞ ሀሳቡን አካፍሎናል።
ዋልያዎቹ ዛሬ ምሽት አንድ ሰዓት ላይ ከአዘጋጇ ሀገር ካሜሩን ጋር ከሚያደርጉት ጨዋታ አስቀድሞ በ2013 የደቡብ አፍሪካዉ የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ቡድኑን ከአሰልጣኝ ሰዉነት ቢሻዉ ጋር መምራት የቻለዉ እና የወቅቱ የፋሲል ከነማ ዋና አሰልጣኝ ስዩም ከበደ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድኑ ዙሪያ ከሀትሪክ ድህረገጽ ጋር በነበረዉ ቆይታ ሰፋ ያለ ጥልቅ ሀሳቡን አካፍሎናል። በተለይ ከዋልያዎቹ አጨዋወት ጋር በተያያዘ ልንከተላቸው ይገባል ስለሚላቸዉ ታክቲካዊ ሀሳቦች እንዲህ ብሎናል።
- ማሰታውቂያ -
ሀትሪክ :- በመጀመሪያ አጠቃላይ ስለ ብሔራዊ ቡድናችን እንዲሁም ስለ እሁዱ ጨዋታ ምን አይነት አስተያየት አለህ ?
ስዩም :- በመጀመሪያ ደረጃ ብሔራዊ ቡድኑን ጠብቀነዉ የነበረዉ ምንም እንኳን ጠንካራ ምድብ ዉስጥ የሚገኝ ቢሆንም በአለም ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታዎች ወቅት ከጋና እና ከደቡብ አፍሪካ ጋር የነበራቸውን እንቅስቃሴ በመመርኮዝ ነበር ፤ ነገር ግን ዕሁድ ዕለት ከኬፕ ቨርዴ ጋር በነበራቸዉ ጨዋታ እንደጠበቅነዉ አልነበረም። እንደ አሰልጣኝ የኬፕ ቨርዴን ጨዋታ እንደተመለከትኩት ያሬድ ባየ በቀይ እስከሚወጣ ድረስ የነበረውን ስምንት ያህል ደቂቃ ኳስን ለመጫወት ስንሞክር የነበረዉ በራሳችን የሜዳ ክፍል ነበር የተጋጣሚያችን ኬፕ ቨርዴ ተከላካዮችም በራሳችን የሜዳ ክፍል ላይ ነበሩ ይሄ ማለት ደግሞ ኳስን መስርተን ለመጫወት በምንሞክርበት ጊዜ ራሳችን ላይ ጫና እንዲፈጠር እያደረግን ነበር ከቀይ ካርዱም በኋላ ይሄ ነዉ የቀጠለዉ።
በተለይ ኳስን ከግብ-ጠባቂ ጀምሮ መስርተን ለመጫወት ስንሞክር የነበረ ቢሆንም ዉጤታማ እንድንሆን ካላደረጉን ነገሮች መካከል አንዱ በቀይ ካርዱ ምክንያት ከመሀል ክፍሉ አንድ ተጫዋች በመቀነሱ ነዉ። ይሄ ምን ማለት ኳስን ከተከላካዮች ተቀብሎ ወደ አጥቂዎቸ የሚያደርሰው የመሐል ክፍሉ ላይ በቁጥር አንሰን ስለምንገኝ እንደተፈለገዉ ለመጫወት ተቸግረን ነበር።
በሁለተኛ ደረጃ ደግሞ ኳሱን ተቆጣጥረን ወደ ተጋጣሚ የሜዳ ክልል ለመግባት ከተቸገርን የመስመር ተጫዋቾቻችንን አቡበከር እና አማኑኤልን ታሳቢ ያደረጉ ከኋላ የሚጣሉ ኳሶች አለመኖራቸው እና ተደጋጋሚ ስህተቶችን መኖራቸው ዋጋ አስከፍለዉናል። ለዚህ ደግሞ ተለዋጭ ሌላ አማራጭ መፈለግ ነበረብን። በእግርኳስ በመጀመሪያ ደረጃ ኳስን ለማንሸራሸር ምቹ እና አስተማማኝ የሜዳ ክፍልን መምረጥ አለብህ። በዚህ ምክንያት ዉጤታማ መሆን አልቻልንም።
ሀትሪክ :- ብሔራዊ ቡድኑ ዛሬ ምሽት ካሜሩንን ይገጥማል ለጨዋታዉ ምን አይነት አቀራረብ ቢኖራቸዉ ዉጤታማ ሊሆኑ ይችላሉ ብለህ ታስባለህ ?
ስዩም :- አሁን ላይ በዋነኝነት ብሔራዊ ቡድናችን የማሸነፍ ስነልቦናዉን ለማግኘት በተቃራኒ ቡድን የሜዳ ክፍል ላይ መጫወት መጀመር አለበት። ይሄም ማለት
የዛሬዉ ጨዋታችን ከካሜሩን ጋር ነዉ የኛ አንድ እና አንድ እድላችን አጥቅተን እና አጥቅተን መጫወት ብቻ ነዉ። ምክንያቱም ቀጣዩ ጨዋታችን ከቡርኪናፋሶ ጋር ነዉ። በመክፈቻው ጨዋታ እንደተመለከትኩት ቡርኪናፋሶ እንደ ቡድንም ሆነ በግል ጥሩ ቡድን ነዉ የተሸነፉትም የኋላ ክፍላቸዉ በሰሯቸዉ ጥፋቶች ነዉ። በካሜሩን በኩልም የምሽቱን ጨዋታ ለማሸነፍ የመጨረሻ ሀይላቸዉን እንደሚጠቀሙ አልጠራጠርም ምክንያቱም ከምድባቸዉ አስቀድመዉ ማለፋቸዉን ለማረጋገጥ። ስለዚህ እነርሱ በሙሉ ሀይላቸው አጥቅተው ለመጫወት ስለሚመጡ እኛም ከሜዳችን ወጥተን በተጋጣሚ የሜዳ ክፍል ላይ መጫወት ይኖርብናል።
(Possess has to be positive) የሚል መርሕ አለ አለም ላይ ለምሳሌ በ Possession ኳስ የሚታወቀዉን የጋርዲዮላ ባርሴሎና ብንመለከት ሙሉ የጨዋታ ክፍለጊዜያቸዉን በተቃራኒ ቡድን የሜዳ ክፍል ነዉ የሚሳልፋት ለዛም ነዉ ዉጤታማነታቸዉ ። ነገር ግን ኳስን በራስህ የሜዳ ክልል ዉስጥ የፈለገ ብትቀባበል ወደ ግቡ መድረስ ካልቻልክ ዋጋ ቢስ ነዉ። እንደበቀደሙ የኬፕ ቨርዴ ጨዋታ በራሳችን የሜዳ ክፍል ጊዜ የምናጠፋ ከሆነ ግን ካሜሩኖች ካለቸዉ የፍጥነት ኳሊቲ እንዲሁም የአካል ብቃት ጥንካሬ አንፃር ተፅዕኖ ሊፈጥሩብን ስለሚችሉ በተቻለን አቅም ከሜዳችን ወጥተን አጥቅተን ከተጫወትን ወደ ዉጤት እንመጣለን ብየ አስባለሁ።
ሀትሪክ :- ብሔራዊ ቡድናችንን ተደጋጋሚ የሚሰሩ ስህተቶች ዋጋ እያስከፈሉት ነዉ። ይህ ከምን የመጣ ይመስልሃል መፍትሔውስ ?
ስዩም :- በመጀመሪያ ደረጃ በየጨዋታው መማር አለብን ግዴታ እራሳችን ስህተት እየሰራን ሳይሆን ከሌሎች ስህተት መማር አለብን ። በእርግጥ ሁሉም ተጫዋች ስህተት ይሰራል ነገር ግን ከስህተቱ መማር አለበት ለምሳሌ ካለፈዉ የኬፕ ቨርዴ ጨዋታ ያሬድ ብቻ ሳይሆን ሙሉ የቡድን አጋሮቹ መማር አለባቸዉ ብየ አስባለሁ። ደግሞ በኛ ሀገር ተጫዋቾች ስነ-ልቦና አንድ ስህተት ከሰሩ በኋላ ለማንሰራራት ትንሽ ይከብዳቸዋል።ለዚህም ተደጋጋሚ ስህተት የምንመለከተዉ በስነ-ልቦናዉ ረገድ ጠንካራ ካለመሆን የመጣ ይመስለኛል። በተለይ ተከላካይ እና ግብ-ጠባቂ ላይ የሚሰሩት ስህተት እጅግ ዋጋ የሚያስከፍሉ ናቸዉ 90% ጎል የመሆን ዕድል አላቸዉ። ስለዚህ አንድ እና አንድ መፍትሄው በየጊዜው ከሚሰሩ ከስህተቶች መማር ፣ ጠንቃቃ መሆን ፣ ኦቨር ኮንፊደንስ አለመሆን ነዉ ብየ አስባለሁ።