በቤትኪንግ ኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የሶስተኛ ሳምንት የመጨረሻ ቀን ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ጠንካራዉን ወልቂጤ ከተማ አሸንፏል።
ካለፉት ሁለት የሊጉ ጨዋታዎች አንዱን ተሸንፈዉ አንዱን ደግሞ በአቻ ዉጤት አጠናቀዉ አንድ ነጥብ ብቻ ማሳካት የቻሉት ቡናማዎቹ በጨዋታው የመጀመሪያ ሶስት ነጥባቸውን ለማሳካት ወደ ሜዳ ሲገቡ በተቃራኒው ክትፎዎቹ ያለመሸነፍ ግስጋሴያቸውን ለማስቀጠል ጨዋታቸውን ጀምረዋል።
በተመጣጣኝ የኳስ ፉክክር የጀመረው የሁለቱ ክለቦች ጨዋታም ገና በ12ኛዉ ደቂቃ ላይ ግብ ተስተናግዶበታል። በዚህም አማካዩ አብዱልከሪም ወርቁ ከመቻችቶ ያቀበለዉን ኳስ የመስመር ተጫዋቹ መስፍን ታፈሰ በግራ እግሩ ወደ ግብነት ቀይሮ ቡናማዎቹን መሪ ማድረግ ችሏል።
- ማሰታውቂያ -
ከግቧ መቆጠር በኋላ ሁለቱም ክለቦች በሜዳዉ የመሐል ክፍል ላይ ኳስን ተቆጣጥረው በመጫወት ወደ ተቃራኒ የግብ ክልል ለመግባት ጥረት ሲያደርጉ የነበረ ቢሆንም ያን ያህል ግን ዉጤታማ መሆን አልቻሉም።
በጨዋታው 30ኛ ደቂቃ ላይ ግን ቡናማዎቹ ድንቅ ሙከራን ማድረግ ችለዋል። በዚህም ብሩክ በየነ ከመስመር ተጫዋቹ ጫላ ተሺታ የተሻገረለትን ኳስ ተቆጣጥሮ ወደ ግብ ቢሞክርም ግብ ጠባቂዉ ጀማል ጣሰዉ ተቆጣጥሯታል።
በሙከራ ረገድ የተሻሉ የነበሩት ቡናዎች በድጋሚ በ40ኛዉ ደቂቃ ላጥ ጥሩ አጋጣሚ አግኝተዉ ነበር ፤ በዚህም በጥሩ የአንድ ሁለት ቅብብል ከግራ መስመር በኩል መስፍን ታፈሰ ያሻገረውን ኳስ ጫላ ተሽታ በግንባሩ ገጭቶ ቢሞክርም ግብ ጠባቂዉ እንደምንም አዉጥቶታል።
አጋማሹ ሊጠናቀቅ ሁለት ደቂቃዎች ብቻ ሲቀሩም በቶሎ ኳስ የነጠቁት ወልቂጤዎች አቡበከር ሳኒ ለጌታነህ አቀብሎት አጥቂዉ ሲሞክር በግቡ አናት ላይ የወጣችዉ ኳስ አቆጪ ነበረች ፤ በዚሁ አጋማሽ ተጠናቋል።
ከዕረፍት መልስ በ49ኛዉ ደቂቃ ላይ ቡናዎች አደገኛ ሙከራ በአጥቂዉ ብሩክ በየነ አማካኝነት ማድረግ ችለዉ የነበረ ቢሆንም በግብ ዘቡ ጀማል ጣሰዉ አማካኝነት እንደምንም ወጥቷለች። በክትፎዎቹ በኩል ምንም እንኳን ተደጋጋሚ የግብ ሙከራ ሲያደርጉ ባይስተዋልም አልፎ አልፎ በመልሶ ማጥቃት እና ከቆሙ ኳሶች አንዳች ነገርን ለመፍጠር ሲታትሩ ተስተዉሏል። በዚህም ዉሀብ አዳምስ ከመሀል ሜዳ አካባቢ የተገኘውን ቅጣት ምት ቀጥታ ወደ ግብ ሞክሮ በረከት አማረ እንደምን ሲያወጣዉ በድጋሚ በጨዋታው መጠናቀቂያ ላይ ደግሞ ከቀኝ መስመር በኩል የተሻማዉን ኳስ ጌታነህ ከበደ በግንባሩ በመግጨት ሲሞክር ለጥቂት ኳሷ ወጥታለች። በዚህም ጨዋታዉ በኢትዮጵያ ቡና 1ለ0 አሸናፊነት ተጠናቋል።