ታህሳስ 28 ቀን 2011 ዓ.ም በሀላባ ስታዲየም በሀላባ ከነማ እና በኢትዮጵያ መድን መካከል ሲካሄድ የነበረው የከፍተኛ ሊግ የ1ኛው ዙር የ6ኛው ሳምንት ጨዋታ በዕለቱ በተፈጠረየስፖርታዊ ጨዋነት ችግር በ76ኛው ደቂቃ መቋረጡ ይታወሳል። የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ የመቋረጥ ዕጣ የገጠመው የዕለቱ አርቢትር ከተመልካች በተወረወረ ድንጋይ በመፈንከታቸውና ይሄንንም ተከትሎ አርቢትሩ “ደም እየፈሰሰኝ ነው፤በዚህ ሁኔታ ጨዋታውን መምራት አልችልም”በማለታቸው ጨዋታው መቋረጡ ይታወሳል።
በዕለቱ ጨዋታ የተፈጠረውን ችግር ሲመረምር የነበረው የፌዴሬሽኑ የዲሲፒሊን ኮሚቴ የቀረቀለትን ሪፖርት ከመረመረ በሃላ ከዚህ በታች ያለውን ውሳኔ ማስተላለፋን በኢሜይል ከተላከልን መረጃ ለማወቅ ተችላል።
ፌዴሬሽኑ በሀላባ ከነማ ላይ ያስተላለፈው ውሳኔ ዋና ዋና ነጥቦች
1.150ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት
2.0 ነጥብና 3የግብ ዕዳ እንዲሁም ለተጋጣሚው የኢትዮጵያ መድን 3 ነጥብና 3 ንፁህ ጎል
3.በቀጣይ በሜዳው የሚያደርጋቸውን ሁለት ጨዋታዎች ከ200ኪ.ሜ ያላነሰ ከሜዳው ውጪ እንዲጫወት
4.ጉዳት የደረሰባቸውን የዕለቱ አርቢትር ኤፍሬም ደበሌ በደረሰባቸው ጉዳት ምክንያት ያወጡትን የህክምና ወጪ በደንቡ መሠረት እንዲተኩ
5.በአንቀጽ 80 ተ.ቁ 16 መሠረት የሀላባ ደጋፊዎችን በ30 ቀናት ስፖርታዊ ጨዋነትን እንዲያስተምሩ የወሰነ ሲሆን ከዚህ ውጪ የዕለቱ ኮሚሽነርና ዋና ዳኛ ያቀረቡትን ሪፖርት አስመልክቶ በሊግና በዳኞች ኮሚቴ በኩል እንዲታይ መወሰኑን ፌዴሬሽኑ በኢሜይል ከላከልን መረጃ ለማወቅ ተችላል።
ይሄንን የፌዴሬሽኑን ውሳኔ ተከትሎ የሀላባ ከተማ ምላሽን ለማወቅ ያደረግነው ጥረት በበዓሉ ምክንያትና የክለቡ ሀላፊዎች ስልክ ሊሠራልን ባለመቻሉ ሃሳባቸውን በዘገባው ማካተት አልቻልንም።