በስምንተኛው ሳምንት መርሀ ግብር ወደ ጎንደር ተጉዞ ሽንፈትን የቀመሰው ኢትዮጵያ ቡና እና በሜዳው ባህርዳር ላይ ሶስት ግብ በማስቆጠር ማሸነፍ የቻለውን ሲዳማ ቡናን ያገናኘው የዛሬው መርሀ ግብር በርካታ ክስተቶችን በማስተናገድ በኢትዮጵያ ቡና ሁለት ለአንድ ማለቅ ችሏል።
ያለወትሮው የአዲስ አበባ ስታድዮም በርካታ ባዶ መቀመጫዎችን አስተናግዶ የተጀመረው የሁለቱ ቡናዎች ጨዋታ በመጀመሪያዎቹ 20 ደቂቃዎች ሲዳማ ቡናዎች የካሳዬ አራጌ ኢቲዮጵያ ቡና ከግብ ጠባቂ ኳስን መስርቶ ለመውጣት እንደሚሞክር በመረዳት ተጫዋቾችን በኢትዮጵያ ቡና ሜዳ ላይ በርከት ብለው እንዲገኙ በማድረግ ጫና በመፍጠር ባለሜዳዎቹ ኳስን እንዳይመሰርቱ የተሳካ እንቅስቃሴ ማድረግ ችለው ነበር።
በአንፃሩ ኢትዮጵያ ቡናዎች የመስመር አጥቂዎቻቸውን ሀብታሙ እና ሚኪያስን ወደ መስመር በማስጠጋት ሜዳውን በመለጠጥ ለመጫወት ሲሞክሩ የተስተዋሉ ሲሆን ሆኖም ይህ ነው የሚባል የማጥቃት እንቅስቃሴዎችን መመልከት አልቻልንም ነበር። በተጨማሪም ኳስን ለመመስረት ቁልፍ ሚና መጫወት የነበረበት የአማካኝ ተከላካዩ አለምአንተ ካሳ ሜዳውን በሚገባው በአይኑ ያለመዳሰስ ችግሩ ኳሶች እግሩ ስር ከገቡ በኃላ የሚወስናቸው ውሳኔዎች ውጤታማ እንዳይሆኑ ሲያደርግበት ተመልክተናል።
- ማሰታውቂያ -
እስከ 35ኛው ደቂቃ እጅግ ለግብ የቀረበ ሙከራ ሆኖ መመዝገብ የቻለችው እንዳለ ደባልቄ (ካክሽ) ከቀኝ መስመር የተሻገረችለትን ኳስ በቄንጥ ወደ ግብ የሞከረው ኳስ ብቻ ናት።
ከመጀመሪያው አጋማሽ መጠናቀቅ አስቀድሞ የኢትዮጵያ ቡና ቡድን ፍፁም ቅጣት ምት ማግኘታቸውን ተከትሎ የሲዳማ ቡና ተጫዋቾች ያልተገባ ባህሪን ሲያሳዩ ተስተውላል::
የተገኘችውን ፍፁም ቅጣት ምት እንዳለ ደባልቄ በማስቆጠር ኢትዮጵያ ቡናን መሪ ማድረግ ችሏል ::
በሁለተኛው አጋማሽ ሲዳማ ቡናዎች በፈጣን አጨዋወት ሲገቡ ፍሬያማ ሆነውም ታይተዋል ::
በእለቱ በሲዳማ ቡና በኩል ጥሩ ሲንቀሳቀስ ያመሸው ዳዊት ተፈራ አቻ ያደረገቻቸውን ጎል ከመረብ ላይ ማሳረፍ ችሏል ::
ከጎሉ መቆጠር በኃላ ኢትዮጵያ ቡና ይበልጥኑ ኳስን በመያዝ በተጋጣሚ የማጥቃት ክልል ላይ ሲደርሱ ሲስተዋል ከስምንት ደቂቃዎች በኃላም በጨዋታው ትልቅ ጫናን ሲፈጥር የነበረው ሀብታሙ ታደሰ ከማእዘን የተሻማውን ካስ በጭንቅላት በመግጨት ኢትዮጵያ ቡና ጣፋጭ ሶስት ነጥብ እንዲያገኙ አድርጓል ::
በኢትዮጵያ ቡና በኩል በሁለተኛው አጋማሽ በቀኝ መስመር ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረው እና ለቡድኑ የማጥቃት እንቅስቃሴ ቁልፍ ሚናን እየተጫወተ የነበረው ሚኪያስ መኮንን በጉዳት ተቀይሮ ሲወጣ ጉዳቱ ለምን ያህል ጊዜ ከሜዳ ሊያርቀው እንደሚችል የተገለፀ ነገር የለም::
ኢትዮጵያ ቡና ድሉን ተከትሎ በአስራ ሁለት ነጥብ ስምንተኛ ደረጃን ሲይዝ ሲዳማ ቡና ከነበረበት ደረጃ ዝቅ በማለት በዘጠነኛ ደረጃ ለመቀመጥ ተገዷል።