በኢትየጵያ ፕሪምየር ሊግ የአራተኛ ሳምንት ጨዋታ ዛሬ(ቅዳሜ) ተደርጎ ያለምንም ግብ ተጠናቋል። 11:35 ሲል የተጀመረው የመከላከያ እና አዳማ ከተማ ጨዋታ ተጠናቋል።
13ኛው ደቂቃ ላይ የመከላከያ መስፍን ኪዳኔ ፍፁም ቅጣት ምት ሳጥን ውስጥ ጥሩ የሚባል ኳስ አግኝቶ ሳይጠቀምበት ቀርቷል። 18ኛው ደቂቃ ላይ የአዳማ ከተማው ምኞት ደበበ ከፍፁም ቅጣት ምት ሳጥን ውጪ የሞከረው ኳስ ወደውጭ ወጥቷል። ብዙው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ በአዳማ የቀኝ ክፍል ያዘነበለ ሲሆን የአዳማ ከተማው ሱራፌል ዳኛቸው ድንቅ ሆኖ ማምሸት ችሏል። 24ኛው ደቂቃ ላይ የመከላከያው ሙሉቀን ደሳለኝ ሳይታሰብ ተከላካዮችን በግሩም ሁኔታ አታሎ የሞከረውን ኳስ የአዳማ ከተማ ግብ ጠባቂ ጃኮ ፔንዞ በቀላሉ ይዞታል። የመጀመሪያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ 3ደቂቃዎች ሲቀሩት ሱራፌል ዳኛቸው አክርሮ መቶት የግቡን ቋሚ ታኮ የወጣው ኳስ የሚያስቆጭ አጋጣሚ ነበር።
በሁለተኛው አጋማሽ መከላከያዎች ወደራሳቸው የግብ ክልል አፈግፍገው አልፎ አልፎ በመልሶ ማጥቃት ወደ አዳማ ከተማ የግብ ክልል ለመድረስ ጥረት ሲያደርጉ ተስተውለዋል። የአዳማ ከተማዎቹ ሚካኤል ጆርጅ እና ከነዓን ማርክነህ በተከታታይ የሞከሯቸው ኳሶች በግቡ አናት ላይ ወጥተዋል።
58ኛው ደቂቃ ላይ የመከላከያው ምንይሉ ወንድሙ ከ40 ሜትር ላይ የተገኘውን ቅጣት ምት ያሻማል ተብሎ ሲጠበቅ በቀጥታ ወደ ጎል ሞክሮት ለጥቂት በግቡ አናት ላይ ወጥቷል። እየቀዘቀዘ የወረዳው ጨዋታ 70ኛው ደቂቃ ላይ በጨዋታው ድንቅ ሆኖ ያመሸው ሱራፌል ዳኛቸው ከሚካኤል ጆርጅ የተሻገረለትን ኳስ ሞክሮት የመከላከያው ግብ ጠባቂ ይድነቃቸው ኪዳኔ በድንቅ ሁኔታ ይዞበታል። ጨዋታው ሊጠናቀቅ 1ደቂቃ ሲቀረው የመከላከያው ግብ ጠባቂ ይድነቃቸው ኪዳኔ የሰራውን ስህተት አላዛር ፋሲካ አግኝቶት ሳይጠቀምበት ቀርቷል።
ከጨዋታው መጠናቀቅ በኀላ የሁለቱም ቡድን አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የመከላከያ አሰልጣኝ ሻ/ል ምንያምር ፀጋዬ “የዛሬው ጨዋታ ከሁለት ጨዋታዎች ሽንፈት በኋላ የመጣ ስለሆነ ልጆቼ ውጥረት ላይ ነበሩ። እንደ ቀደሙት ጨዋታዎች ብዙ የግብ እድል አለመፍጠራችን 3ነጥብ እነሸዳናስመዘግብ አድርጎናል። ያሉብንን ስህተቶች አሻሽለን ቀጣይ ጨዋታዎችን ለማሸነፍ ጥረት እናደርጋለን።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።
የአዳማ ከተማው አሰልጣኝ ተገኔ ነጋሽ በበኩላቸው “አጥቅተን ለመጫወት ሞክረናል፤ ያገኘናቸውን አጋጣሚዎች ብንጠቀም ውጤቱ ያማረ ይሆን ነበር። ወደ 4 እና 5 የሚሆኑ ተጫዋቾች ተጎድተውብናል። እነሱ ሲድኑ ጠንካራውን አዳማን ትመለከታላቹ።” በማለት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።