በ2009 የኢትዮጵያ ኘሪሜየር ሊግ መልካም ግዜን ሳያሳልፍ ወደ ከፍተኛ ሊግ ወርዶ በመወዳደር ላይ የሚገኘው ጅማ አባቡና አንጋፋውን አሰልጣኝ ግርማ ሐብተዮሐንስን ባሰናበተ ማግስት የቀድሞ የቡድኑን አሰልጣኝ አንተነህ አበራ (ቲሾ) ወደ ቡድኑ መመለሱ ተሰምቷል።
ጅማ አባቡና በከፍተኛ ሊጉ እያስመዘገብ ከሚገኘው ዝቅተኛ ውጤት በተጨማሪ በፋይናንሱ ረገድ ቀውስ ውስጥ እንደሚገኝ ለክለቡ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ለሀትሪክ ስፖርት ድህረ-ገፅ አስታውቀዋል።
ቡድኑን ለመረከብ የወረቀት ስራዎች ብቻ እንደሚቀሩት የተናገረው አዲሱ አሰልጣኝ አንተነህ አበራ (ቲሾ ) “በቃል ደረጃ ተስማምተናል ሰኞ የውል ስምምነታችንን እንጨርሳለን ክለቡ በፋይናንስ ችግር ውስጥ ያለነው። ጅማ አባቡና ከመጀመሪያ የመሰረትኩት ቡድን ነው። በነፃም ቢሆን እሰራለሁ ብዬ ተነጋግሬ ተስማምቻለሁ። በቀጣይ ቡድኑን ወደ ተሻለ ምዕራፍ ለማደረስ እሰራለሁ።”በማለት ለድህረ-ገፃችን አስተያየቱን ሊሰጥ ችሏል።
አሰልጣኝ አንተነህ አበራ (ቲሾ) ከዚህ ቀደም ጅማ አባቡና ፣ጅማ ከነማ(አባጅፋር)፣ከፋ ቡናን ማሰልጠኑ የሚታወስ ነው።
- ማሰታውቂያ -
ጅማ አባቡና በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ በምድብ-ለ 10ጨዋታዎችን አድርጎ በ15 ነጥብ በደረጃ ሰንጠረዡ 8ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።