በመሸሻ ወልዴ (ጂቦይስ)
ኢትዮጵያ ቡና በእዚህ ዓመት
ለሚያደርገው የእግር ኳስ ውድድር የቅድመ
ዝግጅቱን ልምምድ መቀመጫውን ዝዋይ /
ባቱ/ ከተማ ላይ በማድረግ በቀን ሁለት
ጊዜ መስራት የጀመረ ሲሆን በእስካሁኑም
ቆይታው ጠዋት ጠዋት ከ12 ሰዓት እስከ
2 ሰዓት እንደዚሁም ደግሞ ቀን ቀን ከ10
ሰዓት እስከ 12 ሰዓት በሚያከናውነው ከኳስ
ጋር የተያያዘ ልምምዱ የቡድኑ በርካታ
ተጨዋቾች መደሰታቸውን እየተናገሩ
ይገኛል፡፡
የኢትዮጵያ ቡና እግር ኳስ ክለብ
በአዲሱ የቀድሞው አሰልጣኙና ተጨዋቹ
በመመራት እየሰራ ባለው የእስካሁኑ
ልምምድ 9 የሚደርሱ የቀድሞ ተጨዋቾቹ
ከቡድኑ በመቀነሳቸው አብረው የማይገኙ
ሲሆኑ ከእነሱም መካከል ዳንኤል ደምሴ፣
ሄኖክ ካሳሁን፣ ተካልኝ ደጀኔ፣ ተመስገን
ዘውዱ፣ አብዱልባሲጥ፣ ፍፁም፣ ቢኒያም እና
የኋላሸትን የመሳሰሉ ተጨዋቾች የሚገኙበት
ሲሆን ምንአልባትም በቀሪው የዝግጅት
ወቅትም ጥቂት ተጨማሪ ተጨዋቾች
ሊኖሩበት ይችላል ተብሎም ከክለቡ አካባቢ
መረጃዎች እየወጡም ይገኛል፡፡
ከኢትዮጵያ ቡና ጋር በተያያዘ ክለቡ
በዝዋይ /ባቱ/ እያደረገ ባለው ዝግጅቱ
አሰልጣኝ ካሳዬ አራጌ የክለቡን ታታሪና
ተወዳጅ ተጨዋች እያሱ ታምሩን አሁን
ላይ የቡድኑ ካፒቴን አድርጎ የሾመ
ሲሆን የተጨዋቾችን አጠቃላይ ጉዳዮችና
ሁኔታዎችን በተመለከተም ከእያሱ ጋር
በመነጋገር መመሪያዎች እንዲተላለፉ
የሚያደርግ ይሆናል፤ እያሱ ታምሩ ከቡና
ጋር ቀሪ የውል ዓመታት ያለው ተጨዋች
ነው፡፡
ኢትዮጵያ ቡናን አስመልክቶ ሌላ
ያለው መረጃ በክለቡ ቀሪ የአንድ ዓመት
ውል ያለውን ተወዳጁን የክለቡን ተጨዋች
አማኑኤል ዩሃንስን ለተጨማሪ አንድ አመት
ለማስፈረም የነበረው ሙከራ ሳይሳካ ቀርቷል፤
ኢትዮጵያ ቡና በሰኔ ወር መጨረሻ ውሉን
የሚያጠናቅቀውን አማኑኤልን ለቀጣዩ ዓመት
ለማስፈረም ሞክሮ ያልተሳካለት ከወርኃዊ
የደመወዝና የፊርማ ክፍያ ጋር ሊስማሙ
ባለመቻላቸው እንደሆነም ከክለቡ አካባቢ
ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡