የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን / ዋልያዎቹ/ በካሜሮን አስተናጋጅነት ለሚካሄደው የቻን
አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የመጀመሪያ
የማጣሪያ ጨዋታቸውን እያደረጉ
ሲሆን በእዚህም የቅድሚያ ግጥሚያ
ከጅቡቲ አቻቸው ጋር ተፋልመው
በአስቻለው ታመነ ብቸኛ የፍፁም
ቅጣት ምት ጎል 1ለ0 ማሸነፍ
ችለዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የመሀል
ሜዳ ተጨዋች የሆነው ሙሉዓለም
መስፍንም /ዴኮ/ ዋልያዎቹ
ጅቡቲን ካሸነፉ በኋላም በዕለቱ
ስለነበረው የጨዋታ እንቅስቃሴና ስለ
ብሔራዊ ቡድኑ እንደዚሁም ደግሞ
በአንድአንድ መድረኮች ላይ በአሁን
ሰዓት ኢትዮጵያን ኳስ ተጨዋቾች
የቴክኒክ ብቃት የላቸውም ስለመባሉና
ሌሎችንም ተያያዥ የሆኑ ጥያቄዎችን
አጠር ባለ መልኩ ጋዜጠኛ መሸሻ
ወልዴ /GBOYS/ አንስቶለት ምላሹን
ሰጥቷል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የጅቡቲ
አቻውን ስላሸነፈበት ጨዋታ
“የጅቡቲ ብሔራዊ ቡድንን በአፍሪካ
የቻን ማጣሪያ ጨዋታ ገጥመን ድል
ያደረግንበት የዐርብ ዕለቱ ጨዋታ በዕለቱ
ከነበረው ከፍተኛ ሙቀት እና እነሱም
በእግር ኳሳቸው ላይ ከፍተኛ መሻሻልን
ከማሳየታቸው አንፃር ሁሉንም ነገር
ተቋቁመን ግጥሚያውን ለማሸነፍ
ብንችልም ጨዋታው ፈታኝ ነበር፤ የጅቡቲ
ተሻሽላ መምጣትም በቀላሉ እንዳናሸንፋትም
ያደረገን ጨዋታም ነበር”
የኢትዮጵያና የጀቡቲ ብሔራዊ ቡድኖች
በሁለቱ 45 ደቂቃዎች ሜዳ ላይ ስለነበራቸው
እንቅስቃሴ
- ማሰታውቂያ -
“የጅቡቲ ብሔራዊ ቡድንን በተፋለምንበት
የዐርብ ዕለቱ ጨዋታ በመጀመሪያው አጋማሽ
የነበረን የሜዳ ላይ እንቅስቃሴ ጅቡቲዎች
ኳሱን በከፍተኛ ፍላጎት ከመጫወታቸው
እና በኳሱም ላይ ለውጥን እያሳዩ
ከመምጣታቸው አኳያ እንደዚሁም ደግሞ
የሙቀቱ መጠንም 43 ድግሪ በመድረሱ
ቡድናችን ጥሩ ሊንቀሳቀስ ያልቻለበት
ነበር፤ በእነሱ በኩል ደግሞ ወደ እኛ የሜዳ
ክልል ለመግባት ወደፊት ፕሬስ አድርገው
ይጫወቱ ነበርና በእዚህ አጋማሽ ቡድናችን
ሊቸገር ችሏል፤ የሁለተኛው አጋማሽ ላይ
ደግሞ ቡድናችን በአንፃራዊነት ተደጋጋሚ
የግብ እድሎችን በመፍጠር በኩል ከጅቡቲ
ተሽሎ የታየበትን ነገር ለማሳየት ቢችልም
በአቋም ደረጃ እነሱም እንደቀድሞው ደካማ
ሆነው አልቀረቡምና ቡድናችን ጨዋታውን
በቀላሉ እንዳያሸንፍም ሊያደርገው ችሏልና
በአጠቃላይ የጨዋታ እንቅስቃሴም የዐርብ
ዕለቱ ጨዋታን ተመጣጣኝ የሆነን ፉክክር
የተመለከትንበትም ነበር”፡፡
ከጅቡቲ ጋር እሁድ ስለሚደረገው
የመልስ ጨዋታ
“የጅቡቲ ብሔራዊ ቡድንን በሳምንቱ
የመጨረሻ ቀናት የምንፋለምበት ጨዋታ
ግጥሚያውን በሜዳችን ከማድረጋችን አኳያ
ከአንድ እና ከሁለት ጎሎች በላይ በማስቆጠር
የምናሸንፍበት ሲሆን ከውጤቱ ባሻገር
በሜዳ ላይ እንቅስቃሴም ጥሩ አቋማችንን
የምናሳይበትም ነው የሚሆነው”፡፡
ጅቡቲን ካለፉ ሩዋንዳን በቀጣይነት
ስለሚፋለሙበት ጨዋታ
“ከጅቡቲ ብሔራዊ ቡድን ግጥሚያችን
በኋላ ሩዋንዳን ስለምንገጥምበት ጨዋታ
ከወዲሁ ብዙ ነገሮችን እያሰብን ነው
የምንገኘው፤ የመጀመሪያ እሳቤያችንም
ለግጥሚያው ሰፋ ያለ ዝግጅትን ከወዲሁ
ስለማድረግ ነው፤ ለጅቡቲው ያለፈው
ጨዋታ የቡድናችን ተጨዋቾች ከእረፍት
ከመምጣታችን አኳያ በአካል ብቃቱ በኩል
ተቸግረን ነበር፤ በዛ ላይ ብዙዎቹ የተመረጡት
ተጨዋቾችም ለቡድኑ አዲስ ስለሆኑም
ግጥሚያችንን ፈታኝ አድርጎት ነበርና አሁን
ከሩዋንዳ ጋር ላለብን ጨዋታ ከወዲሁ ጥሩ
ዝግጅትን በማድረግ ጨዋታውንም በማሸነፍ
የቻን አፍሪካ ዋንጫ ተሳትፎአችንን እውን
ለማድረግ ከፍተኛ ጥረትን እናደርጋለን”፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የተጨዋቾች
ስብስብን በተመለከተ
“የብሔራዊ ቡድናችን የተጨዋቾች
ስብስብ በአብዛኛው በወጣቶች የተገነባ እና
ኳስንም በከፍተኛ ፍላጎት መጫወት በሚችሉ
ልጆች የተዋቀረ ስለሆነ አሁን ላይ ያለን
ቡድን ጥሩ ነው፤ ስብስቡም በጊዜ ሂደት
ጠንካራ ብሔራዊ ቡድን የሚወጣውም ነው
የሚመስለኝ”፡፡
ለካሜሮኑ አፍሪካ ዋንጫ የማጣሪያ
ጨዋታ ከኮትዲቭዋር፣ ከማዳጋስካርና ከኒጀር
ጋር ስለመደልደላቸው
“በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ጨዋታው ላይ
እንደ ኮትዲቭዋር ከመሳሰሉት ሀገራት ጋር
ልንደለደል መቻላችን ብዙ ነገሮችን አስቸጋሪ
እንደሚያደርግብን ብናውቅም ለጨዋታዎቹ
ከወዲሁ አስቀድመን መዘጋጀት ከቻልንና
ጠንካራ ስራዎችንም መስራት ከቻልን
የማጣሪያ ጨዋታዎቹን ጥሩ በሆነ ውጤት
መወጣት የማንችልበት ምንም ምክንያት
አይኖርም፤ በማጣሪያው ጨዋታ ወቅታዊ
ፐርፎርማንስህ ጥሩ ከሆነና የቤት ሥራህንም
አስቀድመህ በሚገባ መስራት ከቻልክ
ከፊትህ ያሉህን ጨዋታዎች በውጤታማነት
ማጠናቀቅም ትችላለክና እኛም ይሄንን ነው
ከወዲሁ በማሰብ ላይ የምንገኘውና ያኔም
በእግር ኳሱ የሀገራችንን እግር ኳስ 1 ደረጃም
ከፍ የምናደርግበትን ውጤት ማስመዝገብ
የምንችልም ይመስለኛል”፡፡
ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን መጫወት
ስለሚሰጠው ስሜት
“የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተመራጭ
ሆነህ ኳስን መጫወት ስትችል ብዙ ህዝብ
እና ሀገርህንም ወክለህ ስለምትጫወት ያለው
የደስታ ስሜት በጣም ከፍ ያለ ነው፤ ለሀገር
መጫወት ከፍተኛ ክብርም የሚያሰጥ ስለሆነ
እኔ ሁሌም ነው እንደተጨዋችነቴ ራሴንም
በጥሩ ብቃት ላይ ለማስገኘት ዝግጅቴን
የማደርገው”፡፡
በየመድረኩ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን
በተደጋጋሚ ደካማ እንጂ ጠንካራ አይደለም
ስለመባሉ እና ኢትዮጵያኖች የቴክኒክ ችሎታ
የላቸውም ስለመባሉ
“የኢትዮጵያ ተጨዋች የቴክኒክ ችሎታ
የላቸውም የሚለው አባባል እኔን ብዙ
አያስማማኝም፤ ታክቲክ የላቸውም ከሆነ
ግን ወደ እግር ኳሱ ከመጣንበት መንገድ እና
አሰልጣኞችም በታክቲኩ ዙሪያ ካላቸው
የእውቀት ማነስ አኳያ በሚገባን መልኩ
ተገቢ የሆነውን ስልጠና ስለማይሰጡን ያን
የምቀበለው ይሆናል፤ በታክቲኩ ዙሪያ
እኛ ኢትዮጵያውያን ተጨዋቾች አሁንም
እደግመዋለው ብቃቱ የለንም፤ ያላደግንበትንና
በጥሩ መልኩ ያልተማርነውን ነገርም ከየትም
ልናመጣው አንችልምና ለኳሱ እድገታችን
በዚህ ላይ ከወዲሁ በተደጋጋሚና በደንብ
ልንሰራበት ይገባል”፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ መሻሻልና እድገ
ትና እንዲያሳይ ከተፈለገ
“የኢትዮጵያ እግር ኳስን በተመለከተ
በአሁን ሰዓትም ሆነ ቀደም ባሉት ጊዜያት
ካለንበት ዝቅተኛ ደረጃ አንፃር ለውጥና
መሻሻልን እንድናሳይ በተደጋጋሚ ጊዜ ብዙ
ነገሮች ሲባሉ ከርመዋል፤ ከእነዚህም መካከል
በዋናነት ከታች መስራት ቢቻል የሚለው
ቃል ሲደጋገምም ተስተውሏል፤ ያ ብንሰራ
ብንሰራ የሚለው ቃልም ከወሬ የዘለለ
ስላልሆነና ሲሰራበትም ያልታየ ስለሆነ
አሁን ላይም እየተሰራበትም ስላልሆነ ኳሱ
በየጊዜው ወደታች እያሽቆለቆል ይገኛልና
በእዚህ ላይ ቆም ብለን ልናስብ ይገባል፡፡
የኢትዮጵያ እግር ኳስ አሁን ላይ ያለበት
ደረጃ ይታወቃል፤ ምንም ስላልሰራንም ጥሩ
ባልሆነ ስፍራ ላይ ልንቀመጥ ችለናል፤ ያም
ስለሆነ በቅድሚያ በኳሱ ላይ ያለንበትን ደረጃ
እና አቅምም አምነን ልንቀበል ይገባል፤ ከዛም
ባሻገር ኳሳችን አሁን ላይ በብዙ ዘርፈ
ችግሮች ውስጥም የሚገኝና ኳሱም ከብሔርና
ከጎሳ እንደዚሁም ደግሞ ከፖለቲካም ጋር
ተገናኝቶ ሁሉም ነገር በእንቅርት ላይ ጆሮ
ደግፍ ነገር በመሆኑም ከእነዚህ ለእግር
ኳሳችን አደገኛ ከሆኑ ነገሮች በፍጥነት
በመውጣትና እግር ኳሳችንን ሊያሳድጉልን
በሚችሉ ነገሮች ላይ መስራትን ዛሬ ብለን
ከተነሳን ሌሎች ሀገራት የደረሱበት ከፍተኛ
ደረጃ ላይ የማንደርስበት ምክንያት የለም፤
ለእዚህ አንድ ምክንያትም ላቅርብ ዛሬ ላይ /
ያነጋገርነው ትናንት ሰኞ ነው/ እኛ የብሔራዊ
ቡድን ተጨዋቾችና መላው የኢትዮጵያ
ህዝብ ችግኝ እየተከለ ነው፤ ይሄን ችግኝ
የምንተክለው ነገ ደን ወይንም ደግሞ ዛፍ
ይሆናል ብለን ነው፤ በእግር ኳሱም ላይ ዛሬ
ላይ እቅድን ይዘን ተገቢውን ስራ ከሰራን
ነገና ወደፊት ከፍተኛ ደረጃ ላይ ይደረሳልና
ይሄንን ለማግኘት አሁኑኑ ለእግር ኳሳችን
እድገት ልንተጋ እና በጣም ልንለፋም
ይገባናል”፡፡