በመከላከያ የአንድ አመት ውል የነበረው አናጋው ባደግ ያለ ክለቡ ፍቅድ ለወላይታ ድቻ በመፈረሙና ያልተገባ ቃል በመጠቀሙ ይቅርታ ጠይቋል፡፡
አናጋው በተይ ለሀትሪክ እንደተናገረው “የአንድ አመት ውል እንዳለኝ ነግረውኛል ሕጋዊ መሆናቸውም ገብቶኛል ያለነርሱ ፍቃድ ሚዲያ ላይ ወጥቼ በመናገሬ ይቅርታ እጠይቃለሁ” ብሏል፡፡ “ከወላይታ ድቻ አመራሮች ጋር በአካል አውርቻለሁ በደንብ የተረጋገጠ ነገር ሣይኖር ዜናውን የክለቡ ገፅ ላይ አውጥተውታል ሁኔታውን ያጦዘው ይሄ ነው” ያለው ተጨዋቹ “ወላይታ ድቻዎች መልቀቂያ ጠይቀውኝ ውል እንደጨረስኩ በእርግጠኝነት ነግሬያቸው አምነው አስፈርመውኛል፡፡ በቃል ስምምነት ከመከላከያ አመራሮች ጋር ስላወራው እሺ ብለው ይለቁኛል ብዬ ባሰብም ፍቃደኛ አልሆኑም ውል ስላለን መልቀቅም ሆነ መከላከል የነርሱ መብት ነው” ሲል ተናግሯል፡፡
“በአጠቃላይ ክለቡን እወደዋለው የፕሪ ሚየር ሊግ ውል ለከፍተኛ ሊግ አይሰራም ብዬ መናገሬ ሕጉን ካለማወቅ የተደረገ በመሆኑ የክለቡ አመራሮች አሰል ጣኞችና ደጋፊዎችን ይቅርታ እጠይ ቃለሁ” ሲል ለሀትሪክ አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡