የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን 10ኛው የመደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በትናንትናው ዕለት በኢንተርኮንቲነንታል ሆቴል መጀመሩ ይታወሳል። በመጀመሪያ ቀን ውሎው ከተሳታፊዎቹ የተለያዩ መወያያ ርዕሶች እና ጥያቄዎች ተነስተው ምላሽ ሲሰጥባቸው እንደነበር በትናንትናው ዘገባችን መዳሰሳችን ይታወሳል። ዛሬም በሁለተኛው ቀን የጉባኤው ውሎ ከትናንት ለዛሬ የተላለፉ የመወያያ ሀሳቦችን ሲመለከት ውሏል።
ምልዐተ ጉባኤው እንደተሟላ ለማረጋገጥ በተደረገው ቆጠራ ጉባኤው ካሉት 130 አባላት 108 አባላት በስብሰባው ላይ በመገኘታቸው ጉባኤው ተጀምሯል። ከዚህም በኀላ በቀረቡት አጀንዳዎች ላይ ውይይት የተደረገ ሲሆን በቅድሚያ የተነሳው የ2010 በጀት ዓመት እቅድ ነበር። በ 2010 እቅድ ዙሪያ ተሳታፊዎች የተለያዩ አስተያየቶችን አቅርበው እቅዱን በ 91ድጋፍ እና በ5 ድምፅ ተዓቅቦ በማጽደቅ ወደ ቀጣዩ አጀንዳ ተሻግረዋል። በማስከተልም በተሻሻለው አዲሱ የመተዳደሪያ ደንብ ላይ ውይይት የተደረገ ሲሆን በዚህኛውም አጀንዳ ላይ ከተሰብሳቢዎቹ የተለያዩ ጥያቄዎች ተነስተው ተወያይተውባቸዋል። ከተነሱት አስተያየት መካከል ኢትዮጵያ ቡናን የወከሉት መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞ ያነሱት ሀሳብ ተጠቃሽ ነው። መቶ አለቃ ፈቃደ ሲናገሩ “መተዳደርያ ደንብ የሚለዉ ቃል ቀለል ያለ ይመስለኛል። ይሄ እኮ የእግር ኳስ ፌዴሬሽን ሕገ መንግስት ማለት ነዉ እኮ። የምንወያየዉ ስለ ሕገ መንግስታችን ነዉ። ስለዚህ ጊዜ ወስደን ልንወያይበት ይገባል” በማለት በአፅንኦት ተናግረዋል። ። መቶ አለቃ ፈቃደ አክለውም “እኔ የምሰጠዉ ሃሳብ ለሚቀጥለዉ ሥራ አስፈፃሚ ይተላለፍና ጊዜ ወስደን እንየዉ።” በማለት ሀሳባቸውን ቋጭተዋል። ከዚህም በኀላ በዛ ያሉት ሀሳቦች ያተኮሩት የተሻሻለዉ መተዳደርያ ደንብን የማፅደቁ መርሃ ግብር ለሌላ ጊዜ ይተላለፍ በሚለው ሀሳብ ላይ ሲሆን በድጋሚ በተደረገ የድምፅ ብልጫ ውሳኔ ደንቡን የማፅደቅ መርሃ ግብር በአብላጫ ድምፅ ለሌላ ጊዜ ተላልፏል።
በማስከተልም ከትናንት ወደ ዛሬ ስለተላለፈው የሥራ አስፈፃሚዎች ምርጫ የሚካሄድበትን ጊዜ እና ቦታ ስለመወሰን ተወያይቶ ምርጫው ከ45 ቀናት በኀላ በሰመራ እንዲካሄድ በሰፊ ድምፅ ብልጫ ልዩነት ተወስኗል።
ውሳኔው ከመተላለፉ በፊት ግን ስለ ምርጫው መራዘም እና ጠቅላላ ጉባኤው ከአፋር ወደ አ/አ ስለተቀየረበት ምክንያት ገለፃዎች ተደርገዋል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝደንት አቶ ተክለወይኒ አሰፋ ሲናገሩ ትናንት ይተላለፍ ተብሎ የተወሰነዉ ምልዓተ ጉባኤዉ ባልተሟላበት ሁኔታ ነዉ” የሚል ቅሬታ አንስተዉበታል። አቶ ተክለወይኒ አክለውም “ነገር ግን፣ ድምፅ ሲሰጥ የተኬደበት መንገድ ልክ ባይሆንም ዉሳኔዉን አንዴ የኢትዮጵያ ሕዝብ ስለሰማዉ እንቀይረዉ አልልም።” በማለት ሀሳባቸውን ገልፀዋል። የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝደንት አቶ ጁነዲን ባሻ ስለ ጠቅላላ ጉባኤዉ ቦታ መቀየር ሲናገሩ “ጠቅላላ ጉባኤዉ ከአፋር ክልል ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ የመጣበት ጉዳይ ከተለያዩ አካላት ግፊት በመደረጉ ነዉ።” ብለዋል። ነገር ግን እነማን እንደሆኑ ከመግለፅ ተቆጥበዋል። በተጨማሪም አቶ ጁነዲን የጉባኤዉ ቦታ ከሠመራ ወደ አዲስ አበባ በመቀየሩ ለአፋር ክልል የይቅርታ ደብዳቤ መፃፋቸውን እና በፋክስ መላካቸውን ተናግረዋል።
- ማሰታውቂያ -
10ኛዉ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በዚህ ሁኔታ ተፈፅሟል። የምርጫ አስፈፃሚዎች ምርጫ ግን ሳይከናወን ቀርቷል።