የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ነገ ይጀምራል።
የ2012 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ነገ እና ሰኞ በሚደረጉ ጨዋታዎች የሚጀምር ይሆናል። 1990 ጅማሬውን ያደረገው እና 23ኛ አመቱን የያዘው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ነገ እሁድ በሚደረጉ 7ጨዋታዎች የሚጀምር ይሆናል። በ1990 በ8 ክለቦች ጅማሮውን ያደረገው ይህ ውድድር ከ22 አመታት በኋላ ቁጥሩን እጥፍ በማድረግ 16 ማድረስ ችሏል። የዘንድሮውን ውድድር ለየት የሚያደርገው ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌደሬሽን ተላቆ አዲስ በተቋቋመ የሊግ ኮሚቴ መመራቱ ነው። አዲሱ የሊግ ኮሚቴ ካለፉት አመታት አሰራሮች ለየት ባለ መልኩ ሊጉን ለማስኬድ እንዳቀደ በተደጋጋሚ የተናገረ ሲሆን ዋናው ትኩረቱ ግን ስፖርታዊ ጨዋነት ላይ እንደሚሆን አስምሮበታል።
ባለፉት ጥቂት አመታት በተለያዩ ምክንያቶች ከሜዳ ውጪ ጨዋታዎችን ማሸነፍ ከባድ እንደሆነ ማስተዋል ተችሏል። ከነዚ ምክንያቶች አንዱ እና ዋነኛው ዳኞች ላይ እና እንግዳው ቡድን ላይ ጫና በማሳደር እንደሆነ በግልፅ ለማየት ተችሏል። ይህንንም አስመልክቶ አዲሱ የሊግ ኮሚቴ እንደዚህ አይነት መሰል ድርጊቶች በ2012 የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ እንደማይከሰቱ አሳውቆ የስነምግባር ግድፈት የሚታይባቸውን ክለቦች ከውድድሩ እንደሚያግድ ከአሁኑ አሳውቋል።
አብዛኞቹ የሊጉ ክለቦች በአዲስ አበባ በአዳማ እና በመቐለ በተደረጉ የሲቲ ካፕ ጨዋታዎች አቋማቸውን ፈትሸው ወደዚህ ውድድር የመጡ ሲሆን ለዋንጫው እንደሚፎካከሩ አሰልጣኞቹ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። እግርኳስ አፍቃሪውም ከረጅም ጊዜ ጥበቃ በኋላ የሚወደውን ክለብ ስቴዲየም በመገኘት ለመመልከት እንደጓጓ ሀትሪክ ስፖርት ድረገጽ ያነጋገረቻቸው ደጋፊዎች ተናግረዋል።
- ማሰታውቂያ -
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመክፈቻ ጨዋታዎች የሚከተሉት ናቸው።
እሁድ
አዳማ ከተማ ከ ፋሲል ከተማ 9:00
ወልቂጤ ከተማ ከ ቅ/ጊዮርጊስ 9:00
ሰበታ ከተማ ከ ወልዋሎ አ.ዩ 9:00
ወላይታ ዲቻ ከ ሲዳማ ቡና 9:00
መቐለ 70 እንደርታ ከ ሀድያ ሆሳዕና 9:00
ሀዋሳ ከተማ ከ ድሬዳዋ ከተማ 9:00
ሰኞ
ጅማ አባጅፋር ከ ባህርዳር ከተማ 9:00
ስሁል ሽሬ ከ ኢትዮጵያ ቡና 9:00