የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔን ለማስተናገድ ሙሉ ዝግጅት መደረጉን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ገለጸ።
39ኛው የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን መደበኛ ጠቅላላ ጉባዔ መጋቢት 6 እና 7 ቀን 2009 ዓም በአዲስ አበባ የአፍሪካ ህብረት አዳራሽ ይካሄዳል።
የፌዴሬሽኑ ፕሬዚዳንት ጁነዲን ባሻ ከኢዜአ ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደተናገሩት ጉባኤውን በተሳካ ሁኔታ ለማስተናገድ ሙሉ ዝግጅት ተጠናቋል።
- ማሰታውቂያ -
እንደ ፕሬዚዳንቱ ገለጻ ጉባኤውን ለማስተናገድ ፌዴሬሽኑ ከካፍ፣ ከወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር፣ ከውጭ ጉዳይ፣ ከኢሚግሬሽን እንዲሁም ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከታቸው መንግስታዊ ተቋማት ጋር በመተባበር አስፈላጊው ዝግጅት ተደርጓል ብለዋል።
ጠቅላላ ጉባኤው ከ60ኛው የካፍ ምስረታ በዓል ጋር ተያይዞ የአፍሪካ መዲናና የካፍ መስራች በሆነችው ኢትዮጵያ መካሄዱ ተገቢ ነው ብለዋል ፕሬዚዳንቱ።
ይህን ጉባኤ ኢትዮጵያ ስታስተናገድ ከ51 ዓመታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ በመሆኑ ታሪካዊና ልዩ ያደረገዋልም ነው ያሉት።
በዚህ ስብሰባ የካፍ አባል አገራት፣ ዓለም አቀፍ ጋዜጠኞችና ታዋቂ እግር ኳስ ተጫዋቾችን ጨምሮ 500 የሚጠጉ እንግዶች ይገኛሉ ተብሏል።
የፊፋ ፕሬዚዳንት ጃአኒ ኢንፋንቲኖ፣ በዓለማችን ከማራዶኖ ቀጥሎ ሁለተኛው ምርጥ አጥቂ በመባል የሚታወቀው ካሜሮናዊው ሮጀር ሚላና የቼልሲ ኮከብ የነበረው ኮትዲቯራዊው አጥቂ ዲዴየር ድሮጎባን ጨምሮ ሌሎች ታዋቂ እግር ኳስ ተጫዋቾች ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።
ጉባኤው በርካታ የሚዲያ ተቋማትና እንግዶች የሚሳተፉበት በመሆኑ ከእግር ኳስም በላይ ለቱሪዝምና ለአገር ገጽታ ግንባታው ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል አቶ ጁነዲን።
ኢትዮጵያ የ2025ቱን የአፍሪካ ዋንጫ ለማስተናገድ ያቀረበችው ጥያቄ ትኩረት እንዲሰጠውና በአዲስ አበባ እየተገነባ ያለው የእግር ኳስ አካዳሚ ግንባታ እንዲፋጠን በማድረግ በኩልም ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ነው ያሉት።
ጉባኤው የካፍ ፕሬዚዳንት ምርጫና ባለፉት 60 ዓመታት የአህጉሪቱ እግር ኳስ ዕድገት ምን እንደሚመስል ውይይት ይካሄድበታል ተብሎ ይጠበቃል።