በደቡብ ደርቢ ሁለቱ የደቡብ ክለቦችን ያገናኝው ጨዋታ በውጤት ቀውስ ውስጥ የሚገኝው አርባምንጭ ከተማ እንዳለ ከበደ ባስቆጠራት ፍፁም ቅጣት ምት 1-0 በማሸነፍ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ማሳካት ችሏል፡፡
በኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር የተጀመረው የመጀመሪያው አጋማሽ ገና በ4 ደቂቃ የዳኝነት ውዝግብን የተመለከትን ሲሆን በረከት ቦጋለ የመጨረሻ ተጫዋቾች ሆኖ በአዲስ ገዳይ ላይ የሰራውን ጥፍት የእለቱ ዳኛ ለሚ ንጉሴ በቢጫ ካርድ ያለፉት አጋጣሚ የሲዳማ ቡና ተጫዋቾችን አስገርሟል::
ቀስ በቀስ ወደ ጨዋታ እንቅስቃሴ የመጡት አዞዎቹ ከእንዳለ ከበደ የተላከለትን ኳስ በተቆጣጠረው ብርሀኑ አዳሙ ላይ ጥፋት በመሰራቱ ፍፁም ቅጣት ያገኙት ባለሜዳዎቹ በእንዳለ ከበደ አማካኝነት የመጀመርያ ጎላቸውን ማስቆጠር ችለዋል፡፡
- ማሰታውቂያ -
ተመስገን ካስትሮ በ21 ደቂቃ እንዲሁም በረከት አዲሱ በ40 ደቂቃ ለጎል የቀረቡ ሙከራዎች ውጪ እንዱሁም ሲዳማ ቡናዎች ከሚያደርጉት የመሀል እንቅስቃሴ በስተቀር ብዙም የጨዋታ ፍሰት ያላየንበት በተደጋጋሚ ተጫዋቾች ተጎድተው ጨዋታው በመቋረጥ የመጀመሪያው አጋማሽ ተጠናቋል፡፡
በሁለተኛው አጋማሽ ተጠናክረው የቀረቡት ተጋባዦቹ ሲዳማ ቡናዎች በተደጋጋሚ የአቻነት ጎል ለማግባት የአርባምንጭ ተከላካይ ክፍልን ሲፈትሹ ቆይተዋል፡፡
ገና በተጀመረ በ48 ደቂቃ ሲዳማ ቡናዎች ያገኙትን ቅጣት ምት ባዬ ገዛኸኝ ወደ ግብ ቢመታውም በአንተነህ መሳ ልትከሽፍ ችላለች፡፡
በተደጋጋሚ ወደ ጎል መድረስ የቻሉት ሲዳማ ቡናዎች በ68 ደቂቃ ከአቡድልለጥፍ መሀመድ የተላከለትን ኳስ በሚያስቆጭ አጋጣሚ ባዬ ገዛኸኝ ሳይጠቀምበት ቀርቷል፡፡ አቡድልለጥፍ መሀመድ፣ባዬ ገዛኸኝ፣አዲስ ገዳይ በግላቸው ያሳዩት አቋም በሜዳው ከተገኙት ተመልካቾች ሙገሳ ተችሯቸዋል፡፡
ባለሜዳዎቹ አርባምንጮች ተበልጠው ባመሹበት ጨዋታ ወደ ፊት ተጭነው ከመጫወት ይልቅ ወደ ሃላ አፈግፍገው መጫወትን መርጠዋል፡፡ ተመስገን ካስትሮ እና ብርሀኑ አዳሙ ከሞከሩት ለጎል የቀረበ ሙከራ ውጪ በተጋጣሚያቸው ሲዳማ ቡና ፊፁም የሆነ የኳስ ብልጫ ተወስዶባቸዋል፡፡ ጨዋታው ሲዳማ ቡና ሙከራ ቢያደርግም የአንተነ መሳን ግብ መድፈር ሳችሉ ቀርተዋል፡፡
ሁለቱም ቡድኖች ይህንን ነጥብ አጥብቀው ቢፈልጉትም እንዳለ ከበደ ባገባት ብቸኛ ግብ ታግዘው አርባምንጭ ከተማ ወሳኝ ሶስት ነጥብ ማስመዝገብ ችለዋል፡፡
የአሰልጣኞች አስተያየት
አሠልጣኝ እዮብ ማለ -አርባምንጭ ከተማ
“ባለፈው ሳምንት በመቐለ ከተማ ሽንፈት መልስ ዛሬ 3 ነጥብ ማግኘታችን የቡድናችንን ስነ-ልቦና ይመልሰዋል። በቀጣይ ጨዋታዎች በበለጠ በማጠናከር ከወራጅ ቀጠናው ስጋት ለመውጣት እንሰራለን።”
አሠልጣኝ ዘርአይ ሙሉ -ሲዳማ ቡና
”በዛሬው ጨዋታ ጥሩ እንቅስቃሴ በማድረግ በአርባ ምንጭ ከተማ ላይ ብልጫ ብንወስድም የዳኝነት ውሳኔ ጥሩ አልነበረም።ለአርባምንጭ ከተማ የተሰጠው ፍጹም ቅጣት ምት ተገቢ ካለመሆኑም በላይ ያልተገባ እንቅስቃሴ በሚያደርጉ ተጫዋቾች ላይ እርምጃ መውሰድ ባለመቻሉ ተጽእኖ ሊፈጥርብን ችሏል፡፡”