የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ዙር ውድድሮች ከሳምንታት እረፍት በኃላ ዛሬ(ቅዳሜ) በተካሄዱ 2 ጨዋታዎች ሲጀምር ነገ(እሁድ) 6 ጨዋታዎችን በማስተናገድ ቀጥሎ ይውላል።በአብዬ ኤርሳሞ ሚካሄደው የሀድያ ሆሳእና ና መቐለ 70 እንደርታ ጨዋታ እንደሚከተለው ዳሰነዋል።
ጨዋታ: ሀድያ ሆሳእና ከ መቐለ 70 እንደርታ
የጨዋታ ቀን: ቅዳሜ የካቲት 28/2012
የጨዋታ ሰዓት: 9:00
የጨዋታ አርቢትር: ኢንተርናሽናል ኣርቢትር ብሩክ የማነብርሃን
የጨዋታ ቦታ: አብዬ ኤርሳሞ ስታድየም
ሀድያ ሆሳእና ከወራጅ ቀጠናው ለመውጣት መቐለ 70 እንደርታ ከመሪዎቹ ላለመራቅ ከፍተኛ ፋክክር ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል።
- ማሰታውቂያ -
የባለፈው ዓመት ክብራቸውን ለማስጠበቅ ከፍተኛ ፋክክር ሚጠብቃቸው መቐለ 70 እንደርታዎች ከሜዳቸው ውጪ ሚያደርጉዋቸውን ጨዋታዎች ማሸነፍ ግድ ሚላቸው ይሆናል። በ8ተኛው ሳምንት ወልቂጤ ላይ ካስመዘገቡት ድል በኃላ ከሜዳቸው ወጥተው ባካሄድዋቸው ሥስት ጨዋታዎች ሽንፈት ያስተናገዱት አሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይለ የቡድናቸውን የማሸነፍ ስነልቦና ለመመለስ ጨዋታውን አሸንፈው ለመውጣት አቅደው ወደ ሜዳ ሊገቡ እንደሚችሉ ይገመታል።
ፊት አጥቂዎቻቸው ላይ መሠረት ባደረገ ቀጥተኛ አጨዋወት በረጅሙ ከመሀል እና ከመስመር በሚነሱ ኳሶች እድሎችን ለመፍጠር ሚሞክሩት መቐለዎች በነገው ጨዋታ የአማኑኤል፣ኦኪኪ እና ያሬድ ከበደ ጥምረት ሚያስፈልገው ይሆናል።በመጀመርያው ዙር የመጨረሻ ጨዋታ በጉዳት ከሜዳ ርቀው የነበሩት ያሬድ ከበደ እና ዮናስ ገረመውን ከጉዳታቸው ያገገሙላቸው መቐለዎች በአፍወርቅ ኃይሉ እና ይሁን እንደሻው ከሚመራው የሀድያ ሆሳእና አማካይ ክፍል ጋር ሚያደርጉት ከፍተኛ ፋክክር የጨዋታውን ውጤት የመወሰን አቅሙ ከፍተኛ ነው።
አሰልጣኝ ፀጋይ ኪዳነማርያምን ከቀጠሩ በኃላ መጠነኛ መነቃቃት እያሳዩ ሚገኙት ሀድያዎች ካንሻበባቸው የወራጅነት ስጋት ለመውጣት ቢያንስ በሜዳቸው ሚያደርጉዋቸውን ጨዋታዎች ማሸነፍ ግድ ይላቸዋል።በግማሽ ዓመት የተጨዋቾች መስኮት ዝውውር ላይ ንቁ ተሳትፎ ያደረጉት ሀድያዎች በነገው ጨዋታቸው የአዳዲስ ፈራሚዎቻቸው ሳሊፍ ፎፎና፣ተስፋዬ አለባቸው ግልጋሎት ሚያገኙ ይሆናል።
ኳሱን ተቆጣጥረው መጫወት ሚችሉ ጥሩ የመሀል ሜዳ ክፍል ተጨዋቾችን የያዙት ሀድያዎች በነገው ጨዋታ መሀል ሜዳ ላይ ብልጫ ወስደው ወደ መስመር በሚወጡ ኳሶች እድሎችን ለመፍጠር ሊሞክሩ እንደሚችሉ ይገመታል።ባሳለፍነው ዓመት ስሑል ሽረን ከወራጅነት እንዲተርፍ ከፍተኛ ድርሻ የነበረውን የቢስማርክ አፒያ፣ቢስማርክ አፖንግ እና ሳሊፍ ፎፎና ጥምረትን ፊት ላይ ሚያገኙት ሀድያዎች እነዚህ ተጨዋቾች የሜዳው መጨረሻ ክፍል ላይ ሚኖራቸው መግባባት የቡድኑ ውጤት ላይ የማይናቅ አስተዋፆ ሚኖረው ይሆናል።