የጨዋታ ቅድመ-ዕይታ | ድሬዳዋ ከተማ ከ ሀዋሳ ከተማ
የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ሁለተኛ ዙር ዛሬ (ቅዳሜ) በተደረጉ ሁለት ጨዋታዎች ጅማሬውን ሲያደርግ ነገ (እሁድ) ደግሞ ቀሪ ስድስት ጨዋታዎች በአዲስ አበባ እና በተለያዩ የክልል ከተሞች የሚካሄዱ ይሆናል። ከነዚህ ስድስት ጨዋታዎች መካከል ነገ የሚደረገው እና ድሬዳዋ ከተማን ከ ሀዋሳ ከተማ የሚያገናኘው ጨዋታ አንዱ ነው።
ድሬዳዋ ከተማ በመጀመሪያው ዙር የሊጉ ጨዋታዎች መልካም የሚባል ጉዞን ማድረግ ተስኖት ተስተውሏል። በተለይ እንደሌሎቹ የሊጉ ክለቦች በሜዳው የሚያደርጋቸውን ጨዋታዎች እንኳን ማሸነፍ ሲቸገር ታይቷል። ለሁለተኛው ዙር ራሳቸውን አጠናክረው ለመምጣት ከፍተኛ ጥረት ሲያደርጉ የቆዩት ድሬዎች 5ተጫዋቾችን በማስፈረም ያሉባቸውን ክፍተቶች ለመሸፈን ሞክረዋል። በሀዋሳ ከተማ በኩል ወጣ ገባ የሚል አቋም የሚያሳይ መሆኑ በጉልህ ታይቷል። ይህም ደግሞ ወደ መሪዎቹ እንዳይጠጋ ከባድ እንቅፋት ሲሆንበት ይስተዋላል። በሀዋሳ ከተማ በኩል ተስፋ የሚጣልበት ወጣቱ አጥቂ ብሩክ በየነ በብዙ ጨዋታዎች ላይ ቡድኑን ሲታደግ በርካታ አድናቆትም ሲጎርፍለት እንደነበር የማይዘነጋ ነው።
ድሬዳዋ ከተማ በሊጉ ባደረጋቸው 15ጨዋታዎች 7ጨዋታዎችን በሜዳው ያከናወነ ሲሆን ከነዚህ 7ጨዋታዎችም 4ቱን በድል ሲያጠናቅቅ በ2ቱ አቻ ተለያይቶ በ1ብቻ ተሸንፏል። በአጠቃላይ ደግሞ 5ጨዋታዎች ሲያሸንፍ በ8ቱ ተሸንፎ በ2ቱ አቻ ወጥቶ በ17ነጥቦች ወራጅ ቀጠና ውስጥ (14ኛ ደረጃ ላይ) ለመቀመጥ ተገዷል።
- ማሰታውቂያ -
ሀዋሳ ከተማ በበኩሉ ተመሳሳይ 7ጨዋታዎችን ከሜዳው ውጪ ያደረገ ሲሆን በ4ቱ ተሸንፎ በ3ቱ ደግሞ አቻ በመለያየት ከሜዳቸው ውጪ ድል ማድረግ ከናፈቃቸው ቡድኖች ውስጥ አንዱ ሆኗል። በአጠቃላይ ደግሞ ከ15ጨዋታዎች 6ቱን በድል ሲያጠናቅቅ በ5ቱ ሽንፈት አስተናግዶ በቀሪዎቹ 4ጨዋታዎች ደግሞ አቻ በመለያየት ማግኘት ከሚገባው 45 ነጥቦች ከግማሽ በታች 22ብቻ ሰብስቦ 6ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል።
በነገው ጨዋታ ድሬዎች ድል የሚቀናቸው ከሆነ የሌሎችን ቡድኖች በመጠበቅ ከወራጅ ቀጠናው ተላቀው እስከ 10ኛ ደረጃ ከፍ ማለት የሚችሉ ሲሆን ሀዋሳ ከተማ ድል የሚቀናው ከሆነ በተመሳሳይ የሌሎችን ክለቦች ውጤት በመጠበቅ እስከ4ኛ ደረጃ ከፍ ማለት የሚችሉ ይሆናል። ሁለቱ ቡድኖች በመጀመሪያው ዙር የመጀመሪያ ሳምንት ተገናኝተው ጨዋታው በሀዋሳ ከተማ 1-0 አሸናፊነት መጠናቀቁ ይታወቃል።