የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ተሳታፊው ክለብ ድሬዳዋ ከተማ በእግር ኳስ ተጨዋችነት ጉዞው ለሙገር ሲሚንቶ፣ ለአዲስ አበባ ከተማ፣ ለጅማ አባቡና፣ ለአዳማ ከተማ እና ለሀድያ ሆሳህና በአጥቂ አማካይ ስፍራ የተጫወተውን ሱራፌል ጌታቸውን በማስፈረም የክለቡ ንብረት አድርጎታል።
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ውስጥ በርካታ ተጨዋቾችን ኮትኩቶ በማሳደግ ከሚታወቀው ሙገር ሲሚንቶ በመገኘት እስከ ኢትዮጵያ ታዳጊ ወጣት እና የኦሎምፒክ ቡድን ለመመረጥ የቻለው ይኸው ተደናቂ ወጣት ተጨዋች ጥሩ ብቃቱን በማሳየት የሚታወቅ ሲሆን ሀድያ ሆሳህና ፕሪምየር ሊጉን እንዲቀላቀልም ትልቁን አስተዋፅኦ ከማበርከቱ በተጨማሪ የከፍተኛ ሊጉ የኮከብ ተጨዋች ምርጫ እጩዎቹ ውስጥም ገብቶ እንደነበር ይታወሳል።
ድሬዳዋ ከተማ ሱራፌልን ያስፈረመው ለአንድ አመት ውል ሲሆን ተጨዋቹ በብርቱካናማዎቹ ማሊያ ጥሩ ጊዜን ያሳልፋል ተብሎም ተጠብቋል።
ድሬዳዋ ከተማ ሱራፌልን ሲያስፈርም ሁለተኛው የክለቡ ተጨዋች ሲሆን ከሐዋሳ ከተማ የመጣው አስጨናቂ ሉቃስ የመጀመሪያው ፈራሚም ሆኗል።