ባለቀለም የስፖርት ጋዜጣ የሆነችው ሀትሪክ ስፖርት በነገው ማክሰኞ መስከረም 30/2010 ዓ.ም እትሟ እንደተለመደው ከሀገር ውስጥና ከባህር ማዶ ትኩስና ወቅታዊ ስፖርታዊ መረጃዎችን ይዛላችሁ ከተፍ ልትል ዝግጅቷን አጠናቅቃ ወደ ማተሚያ ቤት አምርታለች፡፡ ለመሆኑ በዚህኛውስ ዕትም ምን ምን ጉዳዮችን ይዛ ይሆን?
– ከሀገር ውስጥ አዲስ በጀመርነው “Oldies but Goodies” በሚለውና ቀደምት የሀገራችንን ታዋቂ ተጨዋቾችን በምናቀርብበት አምዳችን የቀድሞው የቅ/ጊዮርጊስ እና የብ/ቡድናችን ዝነኛ ተከላካይ የነበረው ብርሃኑ ፈየራ ለጋዜጣዋ ማኔጂንግ ኤዲተር ጋዜጠኛ ይስሀቅ በላይ አስገራሚ ህይወቱን ተርኮለታል፡፡ ከየት ተነስቶ የት እንደ ደደረሰ፣ ስኬቱን፣ የህይወት ውጣ ውረዱን፣ ዕድገትና ውድቀቱን፣ ገጠመኞቹን፣ ከካሳዬ አራጌ ጋር አብረው ባለመጫወታቸው ስለሚሰማው ስሜት፣ ስለ ኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች እና ሌሎችንም ያልተሰሙ ታሪኮችን በግልፅ ይናገራል፤ አንብበው እንደሚረኩበት ምንም አያጠራጥርም፡፡
– ኢንተርናሽናል አርቢትር ሀይለየሱስ ባዘዘው ባለፈው ሳምንት ከጋዜጣችን ጋር ባደረገው አነጋጋሪ ቃለ-ምልልስ ከፌዴሬሽኑ ጋር በድጋሚ ውዝግብ ውስጥ ገብቷል፡፡ ይህንንም ተከትሎ የዲስፕሊን ኮሚቴው የሁለት ዓመት እገዳ እና የ50 ሺህ ብር የገንዘብ ቅጣት እንደ ጣለበት ተነግሯል፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ እሱም ሆነ ጉዳዩ የሚመለከታቸው የፌዴሬሽኑ የአርቢትር ኮሚቴ ሰብሳቢው አቶ ልዑልሰገድ በጋሻው ምላሻቸውን ሰጥተዋል፤ አነጋጋሪነቱ አሁንም ቀጥሏል፡፡
– ቅ/ጊዮርጊስ ከመከላከያ የሚያደርጉትን የአዲስ አበባ ሲቲ ካፕ ግጥሚያ በተመለከተ ከጊዮርጊስ ፍሬዘር ካሳ እንዲሁም ከመከላከያ ሽመልስ ተገኝ ከሀትሪክ ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡ ሌሎችም ተጨማሪ የሀገር ውስጥ ዜናዎችንም ይዘናል፡፡
ከባህር ማዶም ቢሆን ከአራቱ የዓለማችን ታላላቅ ሊጎች ዙሪያ የተገኙ ትኩስና ምርጥ መረጃዎች በብዛትና በጥልቀት ቀርበውበታል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ደግሞ ሌሎች የሀገር ውስጥ አዳዲስ መረጃዎችን ከፈለጉ ድረ ገፃችንን www.hatricksport.com መጎብኘት ይችላሉ፡፡ ነገ ማክሰኞ መስከረም 30/2010 ለንባብ የምትበቃው የሀትሪክ ጋዜጣ የፊት ለፊት ገፅ ይህንን ይመስላል፡፡ መልካም ንባብ!